ገበያው ጎን ካለው፤ ለምሳ ከተመረጠው ምግብ ቤት ደጃፍ መኪናችንን ስናቆም፤ አንድ ሸበቶ አባት ወደ መኪናችን ተጠጉና ከሹፌራችን ጋር በትግርኛ ወግ ጀመሩ። ከሹፌራችን ጋር ለደቂቃዎች ሲጠያይቁ ቆይተው፤ አንድ ነገር ለማሳየት ከደረት ኪሳቸው የማስታወሻ ደብተራቸውን መዘዙ። ለካንስ እንደምንጓዝባት መኪና አይነት ተሽከርካሪያቸው በኤርትራውያን ወታደሮ ተወስዶባቸው፤ በመንገድ ላይ አይተናት እንደሆነ እየጠየቁ ነው። ማስታወሻ ደብተራቸው ደግሞ የመኪናቸው የታርጋ ቁጥር ተመዝግቦ የተያዘባት በመሆኗ፤ ከዚያ ላይ እያነበቡ ለእኛ ለማስገልበጥ ነበር አወጣጣቸው። በአዲግራት የስልክ አገልግሎት ባይኖርም፤ ድንገት በቀጣይ ቀናት ከተከፈተ ያየነውን እንድንነግራቸው ስልክ ቁጥራቸውን አጻፉን።
ብርማ ቀለም እንዳለው የነገሩን መኪናቸው፤ በኤርትራውያን ወታደሮች ከተወሰደ በኋላ እስከ ዕዳጋ ሐሙስ ባለው መንገድ ሲመላለስ እንደከረመ ያዩ ሰዎች ነግረዋቸዋል። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን መኪናውን አየሁ የሚል በመጥፋቱ፤ እንደ እኛ መኪና ሹፌር አይነት ሰው ሲያገኙ እያቆሙ ይጠይቃሉ – “መኪናዬን በመንገድ አይታችኋታል?” እያሉ።
ኤርትራውያን ወስደዋቸዋል ስለሚባሉ መኪናዎች ጉዳይ ብዙ ሰምቻለሁ። ወደ አዲግራት እየመጣን እያለ፤ ሹፌራችን እና የጋራዥ ሰራተኛው አንድ ሲኖትራክ መኪና በመንገድ አይተው እንዴት በመደነቅ ሲነጋገሩ እንደነበር አይቻለሁ። ምን እንዳስገረማቸው ብጠይቃቸው፤ ወደ ኤርትራ ከመወሰድ የተረፈ ሲኖትራክ በማየታቸው እንደሆነ ነግረውኝ ነበር። ሸበቶውን አባት ተሰናበተን ከምግብ ቤት አረፍ እንዳልን ሹፌሩ እና የጋራዥ ሰራተኛው የእነርሱም መኪና ከመወሰድ የተረፈችው በሰዎች ጥረት እንደሆነ እየተቀባበሉ ያጫውቱኝ ገቡ።
በአዲግራት ከተማ እንደልብ የሚንቀሳቀሱ መኪናዎች፤ ኤርትራውያን ከየሰው ላይ የወሰዱት እንደሆነ ሁለቱም አስረድተውኛል። ከምሳ በኋላ ከተማዋን ለማየት ዞር ዞር ባልንበት ጊዜም፤ የከተማይቱ ነዋሪዎች መኪናችንን በጥርጣሬ ሲመለከቱ አስተውያለሁ። በዚህ ሁኔታ መገረሜን ያየው ሹፌራችን፤ በውስጥ ለውስጥ ባሉ መንገዶች መኪናዋን አቁሞ ወጪ ወራጁን ሲያነጋግር፤ የሚያሳዩትን ገጽታ እንድመለከት ጋበዘኝ። ሹፌራችን የትግርኛ ቃላት ሲወረውር፤ በእርግጥም በመኪናዋ ውስጥ ያለነው ሰዎች ኤርትራውያን መስለናቸው ሲደነብሩ አይቻለሁ። እንዲህ ውስጥ ለውስጥ እያሳበረን ወደ አዲግራት ዩኒቨርስቲ የሚወስደው የኮብል ስቶን መንገድ ላይ ወጣን።
Taken from ትግራይ እንዴት ሰነበተች? (የመጨረሻ ክፍል) በተስፋለም ወልደየስ (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)



