በአገሪቱ በተለያዩ አካባቢዎች በሚታዩ ግጭቶችና የፀጥታ ችግሮች ምክንያት፣ አገራዊ ይዘት ያለው ጥናት ማካሄድ እንዳልቻለ የፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት አስታወቀ፡፡
የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር በየነ ጴጥሮስ (ፕሮፌሰር) እንደገለጹት፣ ኢንስቲትዩቱ ቀደም ባሉት ጊዜያት ጥናት ሲያካሂድ፣ ከትግራይ ክልል በስተቀር›› ይባል የነበረ ቢሆንም፣ አሁን ግን ግጭቱ እየሰፋ በመሄዱ በሰፊው የተጀመሩ የምርምር ሥራዎችን ማካሄድ አልተቻለም ብለዋል
"በፀጥታ ችግሩ ምክንያት በአዲስ አበባና በድሬዳዋ ከተሞች ላይ ብቻ ትኩረት ማድረጋቸውን የገለጹት ዋና ዳይሬክተሩ፣ ‹‹ችግሩ በእጅጉ ሥራችን እየተገዳደረ ነው፤›› በማለት አስረድተዋል፡፡
የፕላንና ልማት ሚኒስትሯ ፍጹም አሰፋ (ዶ/ር) በውይይቱ ወቅት እንደገለጹት፣ በሩብ ዓመቱ ከኤክስፖርት ምርቶች 1.2 ቢሊዮን ዶላር ለማግኘት ታቅዶ፣ 814 ሚሊዮን ዶላር ማሳካት መቻሉን ተናግረዋል፡፡
ለዕቅዱ ማነስ ምክንያት በማዕድን ዘርፍ ያለው የፀጥታ ችግርና በግብርና ምርቶች ላይ የሚታየው የሕገወጥ ንግድ መስፋፋት መሆኑን አስታውቀዋል፡፡ በተመሳሳይ ከውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት 1.1 ቢሊዮን ዶላር ለመሳብ ታቅዶ ማሳከት የተቻለው 765 ሚሊዮን ዶላር ነው ብለዋል፡፡
በሩብ ዓመቱ አገሪቱ ማሳካት የቻለችው አጠቃላይ ገቢ 109 ቢሊዮን ብር መሆኑን፣ በሩብ ዓመቱ ለአንድ ሚሊዮን ዜጎች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ታቅዶ ማሳካት የተቻለው 50 በመቶ እንደሆነ ሚኒስትሯ ተናግረዋል፡፡
https://www.ethiopianreporter.com/125119/