በዛሬው ዕለት በሰሜን ሸዋ ዞን ሲያደብርና ዋዩ ወረዳ፣ አባያ ቀበሌ (ሳክላ ምርጫ ጣቢያ) "ልጃቸው የሞተባቸው ወላጆች አስከሬን በቤት አስቀምጠው ታላቅ የዜግነት ኃላፊነት በማሳየት መረጡ" ተብሎ በመንግሥት ሚዲያዎችና በከፍተኛ ኃላፊዎች የተሰራጨው መረጃ፤ ፍጹም ከእውነት የራቀና "በማስገደድ" የተፈጸመ መሆኑን በመግለጽ የተጎጂው ቤተሰብ አባላት በምሬት ተቃውሟቸውን አሰምተዋል።
ከቦታው ለደረሰን መረጃ ምንጭ ሀዘንተኞቹ ቤተሰቦች እንደገለጹት፤ ክሥተቱ በፈቃደኝነት ላይ የተመሠረተ ሳይሆን በጸጥታ ኃይሎች አማካኝነት የተፈጸመ እጅግ ኃላፊነት የጎደለው ድርጊት ነው። ልጃቸው በሞት ተለይቷቸው የቀብር ሥነ-ሥርዓት ለማስፈጸም በዝግጅት ላይ ሳሉ፣ የጸጥታ ኃይሎች በድንገት ወደ መኖሪያ ቤታቸው በመዝለቅ "ምርጫ ካልመረጣችሁ የልጃችሁን አስክሬን አትቀብሩም" የሚል ጥብቅ ትዕዛዝና ማስፈራሪያ ሰጥተዋቸዋል። በዚህም ምክንያት 7 የቤተሰቡ አባላት አስከሬኑን በቤት ውስጥ አስቀምጠው በግዴታ ወደ ምርጫ ጣቢያ እንዲያመሩ ተደርጓል።
ቤተሰቦቹ አክለውም፤ በመንግሥት ባለሥልጣናትና በሚዲያ የሚራገበው ወሬ ሆን ተብሎ ለፖለቲካና ለሚዲያ ፍጆታ ብቻ የተቀነባበረ የሴራ ድራማ ነው ሲሉ አጋልጠዋል። "እንዴት እኛ የገዛ ልጃችንን አስክሬን ቤት አስቀምጠን በደስታ ለምርጫ እንሄዳለን? መሬት ላይ ያለው እውነትና ስቃያችን ሌላ ነው" ሲሉ በከፍተኛ ኀዘንና ምሬት ተናግረዋል።
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ "ይህ ተግባር ሕዝባችን በምርጫው ሂደት ላይ ያለውን ጽኑ እምነት ያረጋገጠበት ሕያው ምስክር ነው" በማለት ያጋሩት መረጃ ፍጹም "ሀሰት" መሆኑን የገለጹት ሀዘንተኞቹ፤ የደረሰባቸው በደልና እውነተኛው ታሪክ ለሕዝብ ይፋ እንዲሆንላቸው ጠይቀዋል።
