-----በኤርትራ ምድር በተፈጸመ አንድ አስገራሚ ታሪክ ዙሪያ ነው የምንቆየው። ይህንን ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ በኢንተርኔት ሳነበው ማመን ከብዶኝ ነበር። ምክንያቱም 18 ሰዎች እንዲያ ዓይነቱን በጀብድ የተመላ ኦፕሬሽን ይፈጽማሉ የሚል ሐሳብ ሊመጣልኝ ስላልቻለ ነው። የደርግ መንግሥት ባለስልጣን የነበሩት አቶ ገስጥ ተጫነ "የቀድሞው ጦር" በሚል ርእስ በጻፉት ዳጎስ ያለ መጽሐፍ ውስጥ ታሪኩን ከዳሰሱት በኋላ ግን እውነት መሆኑን አምኜ ተቀብዬዋለሁ። እናም ያንን ጀብድ በራሴ አቀራረብ ልተርክላችሁ።

የህዝባዊ ግንባር ሓርነት ኤርትራ (ሻዕቢያ) ታጋዮች በትጥቅ ትግሉ ዘመን ከሰማይ ቦምብ እያዘነበ በእንቅስቃሴአቸው ላይ ችግር የፈጠረባቸውን የኢትዮጵያ አየር ሃይል አጥቅተው ከችግሩ ለመገላገል ወሰኑ። በዚህም መሠረት በአስመራ ከተማ ዳር በሚገኘው ሰምበል የተሰኘ የአየር ሃይል ሜዳ ላይ የሚያርፉትን አውሮፕላኖች የሚያወድም ቡድን ያዘጋጁ ጀመር።
ለኦፕሬሽኑ የተመረጡት 16 ታጋዮች ናቸው (ሁለት ታጋዮች በኋላ ላይ ከአስመራ ከተማ ተቀላቅለዋቸዋል)።
ኦፕሬሽኑ ከፍተኛ ጥንቃቄ የሚፈልግ በመሆኑ ለማጥቃት ዘመቻው የተመረጡት ወጣቶች በሙሉ የአስመራ ከተማን መግቢያና መውጫ በደንብ የሚያውቁ እንዲሆኑ ነበር የተወሰነው።

አስራ ስድስቱ ታጋዮች ለኦፕሬሽኑ የሚያስፈልጋቸው የኮማንዶ ስልጠና በሰሜን ኤርትራ በሚገኘው የሳሕል በረሃ ይሰጣቸው ጀመር። ስልጠናውም ሆነ ስምሪቱ በከፍተኛ ጥንቃቄና ሚስጢር መካሄድ ስለነበረበት ከሰልጣኞቹ፣ ከአንዳንድ የሻዕቢያ ወታደራዊ ሃላፊዎች እና ከጥቂት የግንባሩ መሪዎች በቀር ሌሎች የግንባሩ ታጋዮች ስለጉዳዩ የሚያውቁት ነገር አልነበረም።

ኮማንዶዎቹ በዚህ መንገድ ስልጠናቸውን ካጠናቀቁ በኋላ ከሳሕል ተነሱ። እጅግ ሚስጢር በተመላበት ሁኔታ 250 ኪሎ ሜትር ተጉዘው አስመራ ከተማ ዳርቻ ላይ ደረሱ። እዚያ ሲደርሱም በፊት የኮማንዶ ስልጠና የነበራቸውና መረጃ በማሰባሰብ ስራ ላይ የተሰማሩት ሁለት ኮማንዶዎች ተቀላቀሏቸው።
ኮማንዶዎቹ ያሰቡትን ጥቃት ለመፈጸም የያዟቸው መሳሪያዎች AK-47 ጠመንጃ (ክላሽኒኮቭ)፣ ቀላል ቦምብ ማስወንጨፊያ እና የእጅ ቦምቦዎች ብቻ ነበሩ።
እ.ኤ.አ. ግንቦት 21/1984..... May 21, 1984
ምሽቱ አልቆ ውድቅት ነገሷል። በሰምበል አየር ማረፊያ ያሉ የኢትዮጵያ ጦር ሰራዊት አባላት ጥቂት ወታደሮችን በዘበኝነት ከውጪ አቁመው በቤትና በድንኳን ውስጥ ለጥ ብለው ተኝተዋል።
በወታደራዊ አቆጣጠር በ20:00 ሰዓት ላይ ኮማንዶዎቹ የሰንበል አየር ማረፊያን በማጥቃት በነበልባል እና በጭስ ማንደድ ጀመሩ። በአየር ማረፊያው ላይ ያሉ የጦር አውሮፕላኖች በጥይትና በRPG ሲመቱ የሚፈጠረው ፍንዳታ እንደ ብራቅ ጮኸ። የሰንበል ሜዳ በነፍስ ግቢ፣ ነፍስ ውጪ ስሜት በሚተራመሱ ወታደሮች ተመላ። የኢትዮጵያ ሰራዊት አባላት ምን እየተካሄደ እንዳለ እና ማን እንደመጣባቸው ማወቅ ተሳናቸው። አውሮፕላኖቹ ወደ ሚቃጠሉበት ቦታ ለመጠጋት ሲሞክሩ ደግሞ በሻዕቢያ ኮማንዶዎች ተኩስ እየተቀነደቡ ይወድቁ ጀመር።
የሻዕቢያ ኮማንዶዎች በአየር ማረፊያው ላይ ቆመው የነበሩትን 33 አውሮፕላኖች በሙሉ አወደሙ። በአስራ ስምንት ደቂቃ ውስጥ ግባቸውን ፈጽመው ወደ መጡበት ማፈግፈግ ጀመሩ። ይሁንና በስተመጨረሻው ሰዓት "እምባዬ" የተባለው ኮማንዶ ከተቃራኒ ወገን በተተኮሰበት ጥይት ተመትቶ ወደቀ። አስራ ሰባቱ ኮማንዶዎች ግን በድል አድራጊነት ወደ ሳሕል ነጎዱ።

በሰንበል አየር ማረፊያ ላይ የተፈጸመው ጥቃት በደርግ መንግሥት መሪዎች ዘንድ ከፍተኛ ቁጣን ቀሰቀሰ። በማግሥቱ ጓድ ሊቀመንበር መንግሥቱ ኃይለ ማሪያም እሳት ለብሰው፣ እሳት ጎርሰው ወደ ሰንበል አየር ማረፊያ ከች አሉ። ጥቃቱ ወደተፈጸመበት ስፍራ ሲደርሱ በዚያ ያሉት የጦር ሰራዊቱ አባላት በጥቃቱ የወደቀውን ብቸኛውን የህግሓኤ ኮማንዶ አስከሬን በዱላ እየወገሩ እና በሳንጃ እየወጉ ሲጫወቱበት አገኟቸው።
መንጌ ባዩት ነገር በጣም ተናደዱ። ወታደሮቹንም እንዲህ ሲሉ ተቆጧቸው።
"በቶሎ አቁሙ! ወራዳ ሁላ! ይህ ልጅ ላመነበት ዓላማ ተሰውቷል። እናንተ ግን የእርሱን ያህል ለዓላማ መዋጋትን የማታውቁ ውርጋጦችና ልፍስፍሶች ናችሁ። አሁን አስከሬኑን በቶሎ አንሱትና በክብር ቅበሩት"
ከዚያ ጥቃት በኋላ የኢትዮጵያ አየር ሃይል እስከ ናቅፋ እና ቃሮራ ድረስ እየሄደ የሚያደርሳቸው ጥቃቶች በእጅጉ ቀንሰዋል። ኤርትራም ከሰባት ዓመት በኋላ ነፃነቷን ተቀዳጅታለች።









