Ethiopian News, Current Affairs and Opinion Forum
Za-Ilmaknun
Member
Posts: 4307
Joined: 15 Jun 2018, 17:40

የከሰም ስኳር ፋብሪካ ከ3,700 በላይ ሠራተኞቹን ከሥራ አሰናበተ

Post by Za-Ilmaknun » 26 Feb 2025, 11:26

በአፋር ክልል ዱላሳ ወረዳ የሚገኘው ከሰም የስኳር ፋብሪካ፣ በክልሉ እየተከሰተ ባለው ለወራት የቀጠለ ተደጋጋሚ የመሬት መንቀጥቀጥ አደጋ ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰበት ይፋ ባደረገ በወሩ፣ ከ3,700 በላይ ሠራተኞቹን ከሥራ ማሰናበቱ ታወቀ።

በክልሉ በከፍተኛ ደረጃ እየጨመረ በመጣው የመሬት መንቀጥቀጥ አደጋ ምክንያት ተፈናቅለው በካምፕ የተጠለሉ 3,750 ቋሚና ጊዜያዊ የከሰም ስኳር ፋብሪካ ሠራተኞች፣ የካቲት 12 ቀን 2017 ዓ.ም. ባልጠበቁት ሁኔታ ከሥራ መሰናበታቸው ተገልጿል፡፡ በድርጅቱ ማስታወቂያ ሰሌዳ ላይ ስማቸቸው ተለጥፎ ያነበቡበት የስንብት ማሳወቂያ፣ ዕለቱን አስደንጋጭ እንዳደረገባቸው ሪፖርተር ያነጋገራቸው ሠራተኞች ገልጸዋል።

ሪፖርተር የተመለከተው የሰነድ ማስረጃ እንደሚያስረዳው፣ ከሥራ ገበታቸው የተገለሉት 1,250 ቋሚ ሠራተኞች ሲሆኑ፣ የተቀሩት 2,500 ሠራተኞች ደግሞ በሸንኮራ እርሻና በፋብሪካው የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴዎች ላይ አስተዋፅኦ የነበራቸው ጊዜያዊ የሥራ ቅጥር ውል የነበራቸው ሠራተኞች ናቸው።

ከሥራው የተሰናበቱት ሠራተኞች በአፋር ክልል በገቢ ረሱ ዞን በአሚበራ ወረዳ በአዋሽ አርባ ቀበሌ በሚገኝ አዲስ ራዕይ የሚል ስያሜ በተሰጠው የተፈናቃዮች ካምፕ ውስጥ የሠፈሩ ናቸው።

የፋብሪካው ሠራተኞች ባለፉት ሁለት ወራት ከሚጠጋ ጊዜ አንስቶ አዲስ ራዕይ ተብሎ በሚጠራ ካምፕ ውስጥ መግባታቸውን ተናግረዋል፡፡

ከሥራቸው ከተሰናበቱ ሠራተኞች መካከል አንድ ስማቸው እንዳይጠቀስ የጠየቁ ባለትዳርና የሦስት ልጆች አባት፣ ‹‹የሥራ ስንብት ደብዳቤ እንኳን አልተሰጠንም። የሁላችንንም ስም ዝርዝር አንድ ላይ ለጥፈው ነው ተሰናብታችኋል ያሉን። ከዚያም አልፎ ከሁለት ወራት ደመወዝ ውጪ የሚታሰብልን ክፍያ እንደሌለም አሳውቀውናል፤›› ብለዋል።

ግለሰቡ እሳቸውና የሥራ አጋሮቻቸው አደጋ ላይ መውደቃቸውንና ከስኳር ፋብሪካው አመራሮችም ሆነ ከሚያስተዳድረው የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ጉዳዩን በተመለከተ የተሰጣቸው ዝርዝር ማብራሪያ አለመኖሩን ገልጸዋል።

የካቲት 12 ቀን 2017 ዓ.ም. በፋብሪካው ቅጥር ግቢ የተገኙት ሠራተኞች የሥራ ስንብት ማሳወቂያውን ከተመለከቱ በኋላ ግራ መጋባት መፈጠሩንና በፋብሪካው ውስጥ፣ እንዲሁም በእርሻ ሥራ የተሰማሩ ሠራተኞችን ለመለየት በነበረው ጥረት የተወሰነ ግርግር እንደነበር ሪፖርተር ከምንጮች መረዳት ችሏል።

https://www.ethiopianreporter.com/138712/