አዲስ የሚመሠረቱ የፖለቲካ ፓርቲዎች በኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ተመዝግበው “የሙሉ ዕውቅና” የምስክር ወረቀት ለማግኘት ሲጠየቁ የነበረው የ200 ብር ክፍያ ወደ 30 ሺህ ብር አደገ።
በአዲሱ የምርጫ ቦርድ የክፍያ ተመን መሠረት አዲስ የሚቋቋሙ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጊዜያዊ እና ሙሉ የዕውቅና ምስክር ወረቀቶችን ለማግኘት በድምሩ 45 ሺህ ብር መክፈል ይጠበቅባቸዋል።
የፖለቲካ ፓርቲዎችን የመመዝገብ እንዲሁም የመከታተል እና የመቆጣጠር ኃላፊነት በአዋጅ የተሰጠው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ፤ ለሚሰጣቸው አገልግሎቶች የሚጠይቀው ክፍያ ተመን ላይ ጭማሪ ማድረጉን ያስታወቀው ዛሬ ማክሰኞ መስከረም 12/2017 ዓ.ም. ነው።
ከትናንት ሰኞ ጥቅምት 11 ጀምሮ ተግባራዊ የሆነው ይህ የዋጋ ማሻሻያ የተደረገው ቦርዱ ለፖለቲካ ፓርቲዎች በሚሰጣቸው ሦስት አገልግሎቶች ላይ ነው።
የዋጋ ጭማሪ ከተደረገባቸው አገልግሎቶች መከካል አንዱ አዲስ የሚመሠረቱ ፓርቲዎች ከቦርዱ የሚያገኙት የጊዜያዊ እውቅና ምስክር ወረቀት ነው። ይህ ጊዜያዊ እውቅና የሚሰጠው ፓርቲ ለማቋቋም የሚፈልጉ “የዜጎች ስብስብ” ነው።
አገር አቀፍ እና ክልላዊ ፖለቲካ ፓርቲ መመሥረት የሚፈልጉ ግለሰቦች ቢያንስ የ100 ሰዎች ፊርማ የያዘ ቃለ ጉባኤ እና የፓርቲውን ጊዜያዊ ስም እንዲሁም “የምርጫ ሕጉን እና ተያያዥ ሕጎችን የሚያከብሩ ስለመሆናቸው ማረጋገጫ” ሲያቀርቡ ይሰጣቸዋል።

Continue reading https://www.bbc.com/amharic/articles/c8djdy341djo