ዛሬም "የኢትዮጵያ ምድር አንች የደም ጎዳና!"
Posted: 21 Feb 2024, 17:53
በጣም ያሳዝናል::
21 የካቲት 2024, 13:07 EAT
በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን ሞጃ እና ወደራ ወረዳ ሰኞ የካቲት 11/2016 ዓ.ም በአንድ አይሱዙ የጭነት ተሽከርካሪ ላይ በተፈጸመ የድሮን ጥቃት በርካታ ሰዎች መገደላቸውን የዐይን እማኞች እና የአካባቢው ነዋሪዎች ለቢቢሲ ተናገሩ።
ከወረዳው ዋና ከተማ ሰላ ድንጋይ ወጣ ብላ ከምትገኝ ሳሲት ከተባለች አነስተኛ ከተማ የተነሳው ተሽከርካሪው ጋውና መውረጃ ልዩ ስሙ ፈላ መገንጠያ በተባለ አካባቢ ሲደርስ ጥቃቱ እንደተፈጸመበት አራት የቢቢሲ ምንጮች ተናግረዋል።
ስማቸው ለደኅንነታቸው ሲሉ እንዳይጠቀስ የጠየቁ የቢቢሲ ምንጮች በተሽከርካሪው ውስጥ ከ50 በላይ ተጓዦች እንደነበሩ ገምተዋል።
ተሽከርካሪው ተሳፋሪዎችን እያወረደ እያለ ጥቃቱ መፈጸሙን ለቢቢሲ የተናገሩ አንድ የዐይን እማኝ፤ ለክርስትና የወጡ 16 የቅርብ ዘመዶቻቸው መገደላቸውን ገልጸዋል።
“እኔ የማውቃቸው ብቻ የእኔ ቤተሰቦች የሆኑ የአባቴ ወገኖች እና የእናቴ ወገኖች ከ16 ሰው በላይ ሰዎች አልቀዋል... ” ሲሉ የሟቾችን ቁጥር “30 ይደርሳል” ብለዋል።
ጥቃቱ ከረፋዱ 5፡00 እስከ 6፡00 ባለው ጊዜ እንደደረሰ የተናገሩት የአካባቢው ነዋሪዎች ክስተቱን “እልቂት” ሲሉ ነው የገለጹት።
ከሟቾቹ ውስጥ አክስታቸው እና አጎታቸው እንደሚገኙበት የተናገሩ ሌላ የአካባቢው ነዋሪ በጥቃቱ “ሙሉ ቤተሰቦች” እንደተገደሉ ተናግረዋል።
አጠቃላይ የሟቾቹን ቁጥር “30 ይሆናሉ” ያሉ ምንጮች፤ በአያቱ እቅፍ ውስጥ ነበር የተባለው “ክርስትና የተነሳው ህጻን” ጉዳት ሳይደርስበት በሕይወት መትረፉንም ተናግረዋል።
ይህንም አንድ ሌላ የሟቾች ዘመድ ለቢቢሲ አረጋግጠዋል።
“እሱን [ህጻኑን] እግዚአብሔር አተረፈው፤ ምንም አልተነካም” በማለት እናት እና አባቱን ጨምሮ የህጻኑ ሙሉ ቤተሰብ በጥቃቱ መገደላቸውን ገልጸዋል።
በጥቃቱ የተገደሉ ሠዎችን ማንነት የሚጠቅሱ አንድ የኃይማኖት አባት ድምጽ እና ጥቁር ጭስ አይተው ጥቃቱ ወደ ተፈጸመበት ስፍራ ማቅናታቸውን ይናገራሉ።
“ለቅሶ በሆነ ጊዜ፣ ክርስትና በሆነ ጊዜ የዘመድ መኪና እየያዘ ይሄዳል” ሲሉ በአካባቢው ሠው በጭነት ተሽከርካሪ መጓዙ የተለመደ መሆኑን ጠቅሰው ተሽከርካሪው የክርስትና ተጓዦቹ የቤተሰብ ንብረት እንደሆነ ተናግረዋል።
በአካባቢው ሲደርሱም ከህጻናት እስከ አረጋዊያን አስከሬን ማየታቸውን ለቢቢሲ ገልጸዋል።
ጥቃቱ ባጋጠመበት ስፍራ ወዲያውኑ እንደደረሱ የሚናገሩት ሌላ እማኝ “ከፍተኛ አደጋ” ሲሉ ጥቃቱን ይገልጻሉ። በርካታ የቆሰሉ ሰዎች እንዳሉም ተናግረዋል።
የቆሰሉ ሰዎች “20 ይደርሳሉ” ያሉት የኃይማኖት አባቱ፤ ቁስለኞቹ ጋውና እና ሳሲት ጤና ጣቢያዎች መወሰዳቸውን ተናግረዋል።
ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈቀዱ አንድ የጋውና ጤና ጣቢያ ባለሙያ 18 የቆሰሉ ሰዎች ወደ ጤና ጣቢያው ለሕክምና እንደመጡ ለቢቢሲ አረጋግጠዋል። የተሽከርካሪውን ሹፌር ጨምሮ ሦስቱ ቁስለኞች ወዲያ ሕይወታቸው እንዳለፈም ባለሙያው ተናግረዋል።
“ሹፌሩን ጨምሮ እኛ ጋር ሲመጡ በጣም አስጊ ሁኔታ ውስጥ ነበሩ። ያው የተቻለንን ለማገዝ ሞከርን። ህጻናትም አሉ፤ ሹፌሩም አለ። እነሱ ወዲያው ነው ሕይወታቸው ያለፈው” ብለዋል።
ከ15ቱ ቁስለኞች ውስጥ አራቱ ለሪፈራል ሕክምና ወደ ደብረ ብርሃን መጓዛቸውን የተናገሩት ባለሙያው፤ ቀሪዎቹ በጤና ጣቢያው ሕክምና እየተከታተሉ መሆኑን ተናግረዋል።
ጥቃቱ የደረሰበት ስፍራ ላይ በመንግሥት ኃይሎች እና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል ውጊያ እንዳልነበረ የአካባቢው ነዋሪዎች ተናግረዋል።