Port drama failed! No problem. New drama is unvailed!
Posted: 01 Feb 2024, 06:59
Yup! Only electric cars to be imported! Yes, you read that right!
የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስትሩ ዓለሙ ስሜ ይፋ ያደረጉት እና በነዳጅ የሚሠሩ የቤት አውቶሞቢሎች ወደ ኢትዮጵያ እንዳይገቡ የሚከለክለው የመንግሥት ውሳኔ በተሽከርካሪ ገበያው ሥጋት እና ግራ መጋባት ፈጥሯል። ዶክተር ዓለሙ ውሳኔውን የገለጹት ጥር 20 ቀን 2016 በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የከተማ መሠረተ-ልማት እና የትራንስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ፊት ቀርበው የመሥሪያ ቤታቸውን የ6 ወራት የሥራ አፈጻጸም ባቀረቡበት ወቅት ነው።
“ማንኛውም የቤት አውቶሞቢል የኤሌክትሪክ ካልሆነ ወደ ኢትዮጵያ እንዳይገባ መንግሥት ውሳኔ አስተላልፏል” ሲሉ ዶክተር ዓለሙ ለቋሚ ኮሚቴው አባላት ተናግረዋል። መንግሥት ውሳኔውን ካሳለፈባቸው ምክንያቶች አንዱ የኢትዮጵያን የነዳጅ ወጪ ለመቀነስ ነው። ሀገሪቱ በ2015 ነዳጅ ለመሸመት 4.1 ቢሊዮን ዶላር ወጪ አድርጋለች። ይኸ ከዕቃዎች የወጪ ንግድ ካገኘችው ገቢ በ500 ሚሊዮን ዶላር ገደማ የላቀ ነው።
የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ መንግሥት ላሳለፈው ውሳኔ ሁለተኛ ገፊ ምክንያት በተሽከርካሪዎች አማካኝነት የሚደርሰውን የአየር ብክለት መቀነስ ነው። “አዳዲስ ወደ ሀገር ቤት የሚገቡ፤ ሀገር ውስጥ የሚገጣጠሙም የኤሌክትሪክ ብቻ እንዲሆኑ አቅጣጫ ተቀምጧል” ያሉት ዶክተር ዓለሙ ውሳኔው የአየር ብክለትን በመቀነስ ረገድ “የሚያመጣው ለውጥ አለ” ሲሉ ተደምጠዋል።
ወደ ኢትዮጵያ ከሚገቡ ተሽከርካሪዎች አብዛኛዎቹ ለግለሰቦች ጥቅም የሚሰጡ መሆናቸውን የጠቀሱት ሚኒስትሩ “እነዚህን መቀነስ ማለት በአየር ብክለት ላይ የሚደርሰውን ተጽዕኖ በእጅጉ ይቀንሳል” ሲሉ ተናግረዋል።