Page 1 of 1

ኢትዮጵያ ከአጎዋ በመታገዷ ከሐዋሳ ኢንዱስትሪ ፓርክ ብቻ ከአምስት ሺሕ ሠራተኞች ተሰናበቱ

Posted: 28 Aug 2022, 20:17
by sarcasm
ኢትዮጵያ ከአጎዋ በመታገዷ ከሐዋሳ ኢንዱስትሪ ፓርክ ብቻ ከአምስት ሺሕ ሠራተኞች ተሰናበቱ
Ethiopian Reporter


የአሜሪካ መንግሥት ኢትዮጵያን ከአጎዋ (የአፍሪካ ነፃ የገበያ ዕድል) ተጠቃሚነት ማገዱን ተከትሎ ምርታቸውን ወደ አሜሪካ ሲልኩ የነበሩ በሐዋሳ ኢንዱስትሪ ፓርክ የሚገኙ አምራቾች በገበያ ዕጦት ያሰናበቱዋቸው ሠራተኞች ቁጥር ከአምስት ሺሕ በላይ ማለፉ ተገለጸ፡፡

ከኢትዮጵያ ሠራተኞች ማኅበራት ኮንፌደሬሽን (ኢሰማኮ) ያገኘነው መረጃ እንደሚያመለክተው፣ ኢትዮጵያ የአጎዋ ዕድል ተጠቃሚ እንዳትሆን በአሜሪካ መንግሥት ዕገዳ ከተጣለባት ወዲህ በሐዋሳ ኢንዱስትሪ ፓርክ ብቻ አምስት የጨርቃ ጨርቅ አምራቾች በገጠማቸው የገበያ ዕጦት ሠራተኞችን መቀነሳቸውንና በመቀነስ ላይ ይገኛሉ፡፡ በአጎዋ ዕድል ተጠቅመው ወደ አሜሪካ ከቀረጥ ነፃ ምርቶቻቸውን ሲያስገቡ ከነበሩ ኩባንያዎች ውስጥ ሁለቱ ሙሉ በሙሉ ሥራ ያቆሙና ሠራተኞቻቸውን ያሰናበቱ ሲሆን ሦስቱ ደግሞ ሠራተኞቻቸውን ቀንሰው ከማምረት አቅማቸው በታች እያመረቱ ነው፡፡

ሙሉ በሙሉ ሥራ ካቆሙት ኩባንያዎች ውስጥ ፒቪኤች 1,400 እና ቻርቸርስ 22 ሠራተኞች ነበሯቸው፡፡ ቤስት፣ ኤፔክና ኳድራንት የተባሉት ኩባንያዎች ደግሞ ሥራቸውን ሙሉ በሙሉ ባያቆሙም እንደ ቅደም ተከተላቸው 3,000፣ 1,200 እና 161 ሠራተኞች እንደቀነሱ መረጃው ያመለክታል።

በጥቅሉ ከላይ የተጠቀሱት አምራች ኩባንያዎች 5,783 ሠራተኞችን እንደቀነሱ ታውቋል። እነዚህ ኩባንያዎች የተለያዩ የገበያ አማራጮችን በማፈላለግ በአጎዋ ያጡትን ገበያ ወደ ሌሎች አገሮች በመላክ እንዲሁም ታክስ በመክፈል ወደ አሜሪካ ምርቶቻቸውን በመላክ ጭምር እየሠሩ ቢሆንም አሁንም የገበያ እጥረቱ እየፈተናቸው ነው፡፡

ከኢትዮጵያ የጨርቃ ጨርቅ አልባሳትና የመሳሰሉት ሠራተኞች ኢንዱስትሪ ፌዴሬሽን ያገኘው ተጨማሪ መረጃ እንደሚያመለክተውም፣ ከአጎዋ ተጠቃሚነት ዕገዳ በኋላ በተለይ በሐዋሳ ኢንዱስትሪ ፓርክ ውስጥ ያሉ ኩባንያዎች ችግር ውስጥ መሆናቸውንና አማራጭ ገበያ በማጣታቸው ተጨማሪ ሠራተኞች ሊቀነሱ ይችላሉ የሚል ሥጋት አይሏል፡፡

ከገበያ ዕጦት ጋር በተያያዘ እነዚህ ኩባንያዎች በአሜሪካ መንግሥት የተጣለው ክልከላ ካልተነሳ ወይም አዲስ ገበያ የማያገኙ ከሆነ ተጨማሪ የሠራተኞች ቅነሳ ሊያደርጉ የሚችሉ መሆኑንም የፌደሬሽኑ ፕሬዚዳንት አቶ አንገሶም ገብረ ዮሐንስ ሥጋት እንዳላቸው ተናግረዋል፡፡

Continue reading https://www.ethiopianreporter.com/109993/