
ላለፉት ሃምሳ ኣመታት የኣፍሪካ ቀንድ ፖለቲካን እንደ ታላቁ ኢሳይያስ ኣፍወርቂ፣ ውጤታማ ሆኖ ያሽከረከረው ፓለቲከኛ ኣልነበረም ብል ኣልተሳሳትኩም።
የኢሳይያስ ውልደትና እድገት:-
እ.ኤ ኣ በ1946 ዓ.ም መካከለኛ ገቢ ከነበራቸው ቤተሰብ፣ በኣስመራ ከተማ የተወለዱት ኢሳይያስ ኣፍወርቂ፣ በልጅነታቸው ጎበዝ ተማሪ እንደነበሩ ይነገርላቻዋል። በተለይም ደግሞ በማትስና በፊዝክስ የትምህርት ዓይነቶች የሚወዳደራቸው ተማሪ እንዳልነበር ይተረክላቸዋል። የልጅነት ኣብሮ ኣደግ ጓደኞቻቸው እንደሚያስታውሷቸው፣ ኢሳይያስ ሲበዛ እልሀኛና ቂመኛ፣ ደብድበው እንጂ ተደብደብደብው እቤት የማይገቡ፣ በፍጹም ሽንፈትን የማይቀበሉ፣ ነገር ግን በዛው መጠን ትዕግስተኛና ድሃ ሲበደል ማየት የሚጠየፉ ሰው እንደነበሩ ነው። ኣባታቸው ኣፍወርቂ ኣብርሃ፣ የመንግስት ሰራተኛ የነበሩ ሲሆን፣ ወላጅ እናታቸው ኣዳነሽ በርሀ ደግሞ የቤት እመቤት ነበሩ።
ወላጅ ኣባታቸው፣ የኤርትራን ነጻነት አይተው፣ ከዓመታት በፊት ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል። ወላጅ እናታቸው ግን እስካሁን ድረስ በኣስመራ ከተማ በህይወት ይኖራሉ። ወላጅ እናታቸው፣ ዕድሚያቸው 90ዎቹ ውስጥ ቢገባም ኣሁንም ድረስ በእግራቸው ሄደው ቤተ ክርስትያን ይሳለማሉ፣ የቤተሰብ፣ ወዳጅ ዘመድ ሰርግና ቀብር ላይም ይገኛሉ። እኚሁ ወፍራምና ቁመተ ረጅም፣ ባልትና ኣዋቂ፣ መልከ ቆንጆ፣ ቀይ ብስል፣ ደርባባ እመቤት፣ የኢሳይያስ እናት ነኝ ብለው ሲኮፈሱ ኣይታይም። ኣጀብና ሽርጉድ ኣጠገባቸው ላይ ኣይታይም። ከመኖርያ ሰፈራቸው ብቻቸውን ታክሲ ተሳፍረው ዘመድ ጠይቀው ይመለሳሉ። ኢሳይያስ፣ 5 ወንድሞችና ሁለት እህቶች ሲኖርዋቸው፣ ከመጀመርያው ወንድ ልጅ ሁለተኛው ታናሽ ናቸው። በጣም የሚገርመው ደግሞ ሁሉም ወንድምና እህቶቻቸው በርሃ ወርደው ሻዕቢያን ተቀላቅለዋል።
የኢሳይያስ ኣፍወርቂ ኣጭር የትግል ጉዞ ታሪክ:-
እ.ኤ.ኣ በ 1966 በኣዲስ ኣበባ ዩኒቨርሲቲ የኢንጂነሪንግ ኮሌጅ፣ የሁለተኛ ኣመት ትምህርታቸውን ኣቋርጠው Eritrean Liberation Front (ELF) የሚባለውን ድርጅት ተቀላቀሉ። ከሁለት ዓመታት የዩኒቨርሲቲ ቆይታ በኋላም ከሌሎች አምስት ጓዶቻቸው ጋር በመሆን ለከፍተኛ የወታደራዊና የፖለቲካ ስልጠና ወደ ቻይና ተልከው ነበር። ስልጠናቸውን በስኬት ኣጠናቀው ወደ ኤርትራ በረሃ ተመልሰው ትግላቸውን ቀጥለዋል። ይሁን እንጂ ELF ውስጥ የነበረው የትግል ኣካሄድ በመቃወም፣ ከሌሎች ወጣቶች ጋር በመሆን ከELF ተገንጥለው በመውጣት፣ "ሰልፊ ናጽነት" የሚባለውን ድርጅት እዛው ኤርትራ በርሃ ላይ መስርተው፣ ትግላቸውን ቀጠሉ። በኢሳይያስ ይመራ የነበረው ሰልፊ ናጽነት፣ እ.ኤ.ኣ በ1970 ከELF ተገንጥለው ከወጡ ሌሎች ሁለት ድርጅቶች ማለትም ደንከል ላይ ይንቀሳቀስ ከነበረው "ቀዳማይ ወገን ህዝባዊ ሓይልታት" እና "ዑበል" ከተሰኙት ሁለት ድርጅቶች ጋር ከብዙ ውይይት በኋላ ውህደት በመፍጠር፣ "ህዝባዊ ሓይልታት ሓርነት ኤርትራ" በተለምዶ ሻዕቢያ የሚባለውን ዝነኛ ድርጅት በመመስረት ትግላቸውን ኣፋፋሙ።
ኢሳይያስ፣ በረጅሙ የትግል ታሪካቸው፣ በታላቋ ኣሜሪካና በሌሎች ምዕራባውያን መንግስታት ይደገፍ ከነበረውን የኣፄ ሃይለስላሴ መንግስት ጋር ተፋልመዋል። በልዕለ ሃያሏ ሶቪየት ህብረት፣ በኩባና በወቅቱ የሶሻሊስት ምስራቅ ኣውሮፓ ሃገራት በእጅጉን ይደገፍ ከነበረው ወታደራዊው የደርግ መንግስት ጋር እልህ ኣስጨራሽ ጦርነት ኣካሂደዋል። እ.ኤ.ኣ በ1981 ዓ.ም ከኤርትራ ነጻ ኣውጪ ግንባር (ጀብሃ) ጋር መጠነ ሰፊ ጦርነት በመግጠም ኣንጋፋውን ጀብሃ በ6 ወራት ጦርነት ፍርክስክሱን በማውጣት ሱዳን ድንበር ኣሻግረው፣ ድርጅታቸው- ህዝባዊ ግንባር ሓርነት ኤርትራ (ሻዕቢያ) በኤርትራ በረሃ የሚንቀሳቀስ ብቸኛው ድርጅት እንዲሆን ኣደረጉ። ከረጅም ጊዜ እልህ ኣስጨራሽ ጦርነት በኃላ ደግሞ የኤርትራን ነፃነት እውን ኣድርገዋል።
ታላቁ ኢሳይያስ ኣፍወርቂ፣ በምዕራባዊያን መንግስታት በተለይም በኣሜሪካ ይደገፍ የነበረውን የወያኔ ትግሬን መንግስት ከ20 ዓመታት የጦር ሜዳና የዲፕሎማቲክ እልህ ኣስጨራሽ ትንቅንቅ በኋላ ፍርክስክሱን ኣውጥተው ወደ መቃብር ሸኝተውታል። ይሄ ሁሉ ሲሆን ግን ኢሳይያስ ኣንድም ቀን ቴሌቪዥን ላይ ቀርበው ሽለላና ቀረርቶ ሲያሰሙ ኣልታዩም። ጀግና ሰርቶ ያሳያል እንጂ ኣይፎክርም የሚል የቆየ ኣባባል ኣላቸው። ታሪክ ሰሪው ሰፊው ህዝብ እንጂ ግለሰቦች ኣይደሉም ሲሉም ይደመጣሉ። የኢሳይያስ ዝምታ ከንግግርና ከፉከራ በላይ ነው። ለወትሮውም ኢሳይያስ ቴሌቭዥን ላይ ለቃለ መጠይቅ የሚቀርቡት በዓመት ኣንዴ ወይም ቢበዛ ሁለት ጊዜ ብቻ ነው። ጠላቶቻቸውን በስም ፈጽሞ ኣይጠሩም። በጠላቶቻቸው ኣፍ ግን ስማቸው እንደ መዝሙረ ዳዊት ይደገማል። ሁሉንም ጠላቶቻቸውን ቀብረዋል። አረ ገዳይ! ዘራፍ! ማን እንደኔ! ሲሉ ግን ኣይታዩም።
በቅርብ የሚያውቋቸው፣ በኢሳይያስ ዝምታ ውስጥ የሚያስፈራ ድባብ ኣለ ይላሉ። ይህ የኢሳይያስ ውጤት ተኮር ዝምታ ግን ከእርሳቸው ኣልፎ በድርጅታቸው ውስጥ ባሉ ከፍተኛ የወታደራዊና የደህንነት ሃላፊዎችም ላይ ይስተዋላል። ድምፅን ኣጥፍቶ ዝም ብሎ ስራን መስራት የሻዕቢያ ባህል ነው። ኢሳይያስ፣ የሃይማኖትና የብሄር ፓለቲካን በእጅጉ ይጠየፉታል። ኤርትራ ላይ፣ ሃይማኖትንና ብሄርን መሰረት ያደረገ ፖለቲካ ማካሄድ ፈጽሞ የተከለከለ ነው። ያንን ማሰብም እራሱ ከባድ፣ ከባድ፣ በጣም ከባድ ወንጀል ነው።
በኢትዮጵያ ህዝብ ጫንቃ ላይ ተንሰራፍታ ተቀምጣ፣ በምዕራባዊያን ድጋፍ፣ እንቁራሪት ሆና ሳለ፣ ዝሆን ሆና የተሰማትን ወያኔ ትግሬን ኢትዮጵያ ውስጥ ለውጥ ከመምጣቱ ከወራት በፊት እ.ኤ.ኣ ጥር 2018 ላይ ነበር በኣንድ የቃለ መጠይቃቸው ኣጋጣሚ "ወያኔ! Game Over" ብለው መሞቷን በቁሟ ያረዷት።
የኢሳይያስና የድርጅታቸው ትልቁ ጠንካራ ጎን የተዋጣለት የስለላ መዋቅራቸውና የወታደራዊ ቅልጥፍና ብቃታቸው እንደሆነ ብዙዎች ይስማሙበታል። በረጅሙ የበርሃ የትግላቸው ጉዞ፣ ድርጅታቸውን ሻዕቢያ ከውድቀትና ከሽንፈት፣ ከውስጥና ከውጪ ጠላቶቻቸው የታደጉት፣ ሻዕቢያ ውስጥ ሌላ ምስጢራዊ ታማኝ ኣስኳል ድርጅት በማዋቀር ነው። ሻዕቢያ ቅርፊቱ ሲሆን ኣስኳሉ ደግሞ ይሀው ሌላ ምስጢራዊ ድርጅት ነው። "ፈዳይን" ተብለው ይጠሩ የነበሩት ለመሞት የቆረጡ ሴትና ወንድ ወጣት የከተማ ገዳይ ስኳዶችም ውጤታማ ስራ ሰርተዋል። "ሓለዋ ሰውራ" ይሰኝ የነበረውና ሻዕቢያን ከውስጥ ጠላቶች የሚጠብቀው የጸጥታ ተቋምም ውጤታማ ስራ ሰርቷል።
ሻዕቢያ፣ ሳህል በረሃ ላይ ከተራራ ስር ተፈልፍለው የተሰሩ፣ የወታደራዊ ማሰልጠኛ ተቋማት፣ የመድሃኒት ፋብሪካ፣ ሆስፒታል፣ የሬድዮ ጣቢያ፣ ማተሚያ ቤቶች፣ ፖለቲካዊና ወታደራዊ ጽሕፈት ቤቶች፣ በጣም ግዙፍ ጋራጆች፣ የእጅ ስራ ውጤት ማምረቻ፣ የወታደራዊ ዩኒፎርም ማምረቻ፣ የጦር መሳርያ ጥገና ክፍል፣ የመድሃኒት ፋብሪካ፣ የምርኮኞች ጣቢያ፣ የወታደራዊ መገናኛ ራድዮ ክፍል የወታደራዊ ራድዮ ጠለፋ ክፍል፣ የስንኩላን ማገገሚያ፣ የክራንች መስርያ ፋብሪካ፣ የህጻናትና ልጆች መጠለያና ትምህርት ቤቶችን ገንብቶ ነበር። በኣጭሩ፣ ሻዕቢያ መንግስታዊ መዋቅር የነበረው የበርሃ ላይ መንግስት ነበር ለማለት ይቻላል። ኢሳይያስ፣ በረጅሙ እልህ ኣስጨራሽ የትግል ጉዟቸው በርካታ ጊዜያት ከሞት ኣፋፍ ላይ ኣምልጠዋል። የሰው ልጅ እግዜር ባለው ቀን ነው የሚሞተው፣ እኔም ሞትን ኣልፈራም፣ ቀኔ ሲደርስ እሞታለሁ ሲሉ ይደመጣል። የኢሳይያስ መዝገበ ቃላት ውስጥ ተስፋ መቁረጥና ሽንፈት የሚባሉት ቃላት ኣይታወቁም። ከ43 ዓመታት በፊት እ.ኤ.ኣ በ1977 ዓ.ም ላይ ደርግ "የምስራቁ ድል በሰሜን ይደገማል!" በማለት 200,000 ሰራዊት ወደ ኤርትራ ያዘመተበት ወቅት ነበር። በግዜው ሻዕቢያና ጀብሃ ኣስመራን በ12 ኪ.ሜ ርቀት 360° ከበው ዛሬ ወይም ነገ ኣስመራ እንገባለን እያሉ ከነበሩበት ምሽግ ወጥተው፣ ጀብሃ ወደ ባርካ በረሃ፣ ሻዕቢያ ደግሞ ወደ ሳህል ተራሮች እየተዋጉ ስልታዊ ማፈግፈግ በሚያደርጉበት ጊዜ ከረን ከተማ ላይ ዳን ኮኔል የተባለው ኣሜሪካዊ ጋዜጠኛ የሚከተለውን ጥያቄ ያኔ ዕድሜያቸው 31 ዓመት ብቻ ለነበረው ኢሳይያስ ያቀርብላቸዋል:-
"ኣሁን ላይ እያየን እንዳለነው ከኣስመራ ደጃፍ ላይ ነው የተመለሳችሁት፣ የኢትዮጵያ መንግስት ደግሞ ሶማሊያን ኦጋዴን ላይ ድል ኣድርጎ የተመለሰ 200,000 ወታደርና እጅግ ዘመናዊ የሶቪየት ከባድ መሳርያ የታጠቀ ሰራዊት እየዘመተባችሁ ነው፣ እናንተም ይሀው እንደምናየው እያፈገፈጋችሁ ነው፣ መጨረሻችሁ ምን ይሆናል ብለህ ታስባለህ?"
ኢሳይያስ ለዳንኮኔል የሰጠው መልስ የሚከተለው ነበር:-
" The more the enemy challenges me, the more stubborn I become"
ማለትም:- "ጠላት በታገለኝ መጠን እኔም እልሀኛ እሆናለው" የሚል ነበር።
ኢሳይያስ፣ ብዙዎቹን ጠላቶቻቸው በረጅም ጊዜ ማሰላቸት ነው ያሸንፍዋቸው። "ጊዜ ዘይምልሶ ነገር የለን" ማለትም "ጊዜ መልስ የማይሰጠው ነገር የለም" የተለመደ ኣባባላቸው ነው።
ከ 20 ዓመታት በፊት፣ "ወያኔ በተራዘመ ጦርነት ሻዕቢያን ኣሸንፋለሁ እያለ ነውና ለዚህ ምን መልስ ኣለህ" ተብሎ በጋዜጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄ እጅግ በሚያስፈራ የፊት ገጽታ የሚከተለውን ኣጭር መልስ ነበር የሰጡት:-
" ኣብ ዝተናወሐ ጉዕዞ ንሻዕቢያ ክንስዕር ኢና ንዝብልዎ ጉዳይ፣ ደሓነይ፣ ኣብ'ታ ዝብልዋ ዘለው ነዋሕ ጉዕዞ የራኽበና ጥራይ እየ ዝብሎም"
ትርጉሙ:-
ሻዕቢያን በተራዘመ ጉዞ እናሸንፋለን ስለሚሉት ነገር፣ ግድ የለም፣ ረጅሙ መንገድ ላይ ያገናኘን ብቻ ነው የምለው" የሚል መልስ ነበር የሰጡት።
እኛ ታዛቢዎች ደግሞ የ22 ዓመት የፈጀውን የተራዘመ እልህ ኣስጨራሽ የጦር ሜዳና የዲፕሎማሲ ጦርነት (የሻዕቢያና የወያኔ ትግሬ የምስራቅ ኣፍሪካ ደርቢ)፣ በኢሳይያሱ ሻዕቢያ ኣሸናፊነትና በወያኔ ትግሬ መደምሰስ ሲጠናቀቅ በኣይናችን ለማየት በቅተናል።
ኢሳይያስና ሻዕቢያ:-
ኢሳይያስን ከሻዕቢያ፣ ሻዕቢያን ከኢሳይያስ ነጥሎ ማየት ኣይቻልም። መንትያ ቃላት እስኪመስሉ ድረስ ሁለቱም እጅግ የጠበቀ ግንኙነት ኣላቸው። ኣሳይያስን ኣንስቶ ሻዕቢያን፣ ሻዕቢያን ኣንስቶ ኢሳይያስን ኣለማንሳት ፈጽሞ ኣይቻልም።
ኢሳይያስ፣ ሻዕቢያና የኢትዮጵያ ተቃዋሚ ድርጅቶች:-
ወያኔ የተባለው የትግራይ ብሄረተኛ ድርጅት ሲመሰረት፣ ለኣንጋፋ የወያኔ መሪዎች ወታደራዊ ስልጠና የሰጠው የኢሳይያሱ ሻዕቢያ ነው። በሻዕቢያ ወታደራዊ ስልጠና ከተሰጣቸው የወያኔ መሪዎች መካከል ስዬ ኣብርሃና ስዩም መስፍን ይገኙበታል። ሻዕቢያ፣ በኣስር ሺዎች የሚቆጠሩ የወያኔን ጀሌዎችን በተለያየ ጊዜያት ኤርትራ በረሃ በማስመጣት ወታደራዊ ስልጠና ሰጥቷል። ከዚህም በተጨማሪ፣ ወያኔ ኣዲስ ኣበባ ገብቶ የኣራት ኪሎ ቤተመንግስትን እስኪቆጣጠር ድረስ የሻዕቢያ የኮማንዶና የከባድ መሳርያ ሜካናይዝድ ቀጥተኛ ድጋፍ ኣልተለየውም ነበር። የኢሳይያስ ኣፍወርቂው ሻዕቢያ ወያኔን ብቻ ኣይደለም የረዳው። ኦነግ፣ኢህኣፓ፣ የኣፋር ነጻ ኣውጪ ግንባር (ኣነግ)፣ የኦጋዴን ነፃ ኣውጪ ግንባር፣ ኢህዴን ወዘተ የተሰኙ ተቃዋሚ ድርጅቶች፣ በተለያየ ወቅት ከሻዕቢያ ወታደራዊ ስልጠናና የጦር መሳርያ ድጋፍ ያገኙ ድርጅቶች ናቸው። ይህ የሻዕቢያ የወታደራዊ ድጋፍ፣ የወያኔ መንግስትን በወታደራዊ ሃይል ለመጣል ይታገሉ ለነበሩት በርካታ የኢትዮጵያ ተቃዋሚ ድርጅቶችም ቀጥሏል።
በኣፍሪካ ፖለቲካና ታሪክ ላይ ያተኮሩ ከ 30 በላይ የጥናት መጻህፍትን የጻፈው እውቁ እንግሊዛዊ ጋዜጠኛና የታሪክ ተመራማሪ፣ ባዚል ዴቪድሰን (Basil Davidson) ኤርትራ በረሃ ድረስ በኣካል በመገኘት የሻዕቢያን ገድል በቅርብ ካስተዋለ በኃላ፣:-
"EPLF is the most effective guerilla army in the world" ሲል ገልጾታል።
ኢሳይያስ ኣፍወርቂና የግል ባህርያቸው:-
በቅርበት የሚያውቋቸው ሰዎች እንደሚናገሩት፣ ኢሳይያስ ኣፍወርቂ፣ እጅጉን ኣንባቢና ኣሰላሳይ መሆናቸውን ነው። ፓለቲካን በጥራዝ ነጠቅ ምሁርነት ሳይሆን ከነባራዊ ሁኔታ ጋር በማገናዘብ ይጫወቱታል። ለዚህም ሳይሆን አይቀርም፣ መለስ ዜናዊ በኣንድ ወቅት "ኣራት ኣመት ዩኒቨርሲቲ ከመማር፣ ሁለት ሰዓት ከኢሳይያስ ጋር ማውራት ይበልጣል" ሲል የተደመጠው። ኢሳይያስ፣ ውጤታማ ስራ ለመስራት፣ ሌሊት ላይ ከእንቅልፍ የመነሳት ልምድ ኣላቸው። ጠዋት በጣም ወፍራም ቡና መጠጣት ያዘወትራሉ። በአብዛኛው ምግባቸው የገብስ ደረቅ ቂጣ በሽሮ ወይም በምስር ወጥ ነው። የቀይ ባህር ዓሳ በኮተሌቲ መልክ ተሰርቶ ሲቀርብላቸው የሚወዱት ምግባቸው ነው። የኣትክልት ምግቦችንና ጥራጥሬንም ያዘወትራሉ። መጠጥ መጠጣት ካለባቸው የኣስመራ ሜሎቲ ኣረቄን በመጠኑ ይጎነጫሉ። የሜሎቲ ኣረቄን ከመጠጥነቱ ባሻገር ፈዋሽነቱን እየመሰከሩ ይጎነጩታል።
ኢሳይያስ የብዙ ቋንቋ ተናጋሪ (multi-lingual) ናቸው ። የኤርትራ ትግርኛን ይራቀቁበታል። ዓረቢኛውን ይቀኙበታል። እንግሊዘኛውን ይጠበቡታል። ሰውየው፣ በጣልያንኛና ዓረቢኛ ቃላቶች እየተዋዛ የሚነገረውን ዘመንኛ የኣስመራ ኣራዶች ቋንቋ (slung) ሲጠቀሙበት ፈገግ ያስብላሉ። ኢሳይያስ ቀልድና ተረብ ኣዋቂ ናቸው። ለጠላቶቻቸው የሚበቃ፣ በትክክል የሚመጥናቸውን፣ በልካቸው የተሰፋ የኣሽሙርና የተረብ መጠርያ ድሪቶ በማውጣት ኢሳይያስን የሚያህል የለም። የዓረቢኛ ቋንቋ ክህሎታቸው፣ ግብጽ ካይሮ ላይ የሚገኘው፣ የዓለማችን እውቁ የእስልምናና የዓረቢኛ ቋንቋ ጥናት ተቋም የሆነው የኣልሃዛር ዩኒቨርሲቲ ጉምቱ ምሁራንን ያስደመመ ነው። በዚህ የረቀቀ የዓረቢኛ ቋንቋ ችሎታቸው ሳይሆን አይቀርም፣ የዓረቡን ዓለም መሪዎች እንደ ጢባጢቤ ሲጫወቱባቸው የሚታዩት። የኣብዛኞቹን ኣሁን በስልጣን ላይ ያሉት የዓረብ ኣገራት ወጣት ንጉሳዊያን መሪዎች፣ ኣባትና ኣያቶቻቸው ንጉሳዊያን መሪዎች እያሉ ጀምረው ነው ኢሳይያስ ኣብጠርጥረው የሚያውቋቸው። በዓረቡ ዓለም ለኢሳይያስ ኣፍወርቂ በቋሚነት የሚዘጋ በር የለም። ከዓመታት በፊት የየመን ጦርነት ሲቀሰቀስ፣ ወድያውኑ ነበር ሳዑዲ ዓረቢያና የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ ዳጎስ ያለ ገንዘብና የዲፕሎማቲክ ጥቅማ ጥቅሞችን ይዘው የኢሳይያስን ደጅ የጠኑት። ዓረቦችን፣ " ግድ የለም በበር ቢሄዱ፣ በጓዳ ተመልሰው ይመጣሉ" ሲሉ ይዘብቱባቸዋል። ከረጅም ጊዜ የፓለቲካ ልምዳቸው የተነሳም፣ ኢሳይያስ፣ የመካከለኛው ምስራቅና የኣፍሪካ ቀንድ ፖለቲካን እንደ እጃቸው መዳፍ ያውቁታል። ይራቀቁበታል። ከእስራኤል ጋር በጥብቅ ቢወዳጁም በሳውዲ ዓረቢያ ቤተ መንግስት ቀይ ምንጣፍ ሲነጠፍላቸው ይታያል።
ኢሳይያስ፣ የሁለት ወንዶችና የኣንዲት ሴት ልጅ ኣባት ናቸው። ከልጆቻቸው መካከልም ሴት ልጃቸውን ኣብልጠው እንደሚወዱ በኣንድ ቃለ መጠይቅ ላይ ሲናገሩ ተደምጠዋል። ኢሳይያስ፣ ቀለል ያለ ኣጀብ የሌለበት የኑሮ ዘይቤ ይወዳሉ። ቤተ መንግስት ውስጥ ኣይኖሩም። መኖርያ ቤታቸውም መካከለኛ ገቢ ያላቸው ሰዎች ከሚኖሩበት ሰፈር ነው። የጎረቤት፣ ወዳጅ ዘመድ ሰርግ ላይ እንደማንኛውም ሰው ታድመው ይገኛሉ። በእረፍት ጊዚያቸው መኖርያ ግቢያቸው ውስጥ ካለው የእንጨት ስራ ወርክሾፕ ውስጥ የተለያዩ የእንጨት ላይ ቅርጻ ቅርጾችን በመቅረጽ ያሳልፋሉ። ስእል መሳልም ሌላኛው የሚያስደስታቸው ነገር ነው። መደበኛ የኣካል እንቅስቃሴ ስፖርትም ይሰራሉ። በትርፍ ጊዚያቸው ኣብረዋቸው ከሚኖሩ የልጅ ልጆቻቸው ጋር መላፋትና መጫወትም ኣንዱ ከሚያስደስታቸው ነገር ነው።
በቃ ይኸው ነው፣ ኢሳይያስን ማሸነፍ ኣይቻልም!
ፈጽሞ ኣይቻልም!
