የአብይ አህመድ "የመደመር ወይም የማግበስበስ" ፓለቲካ ክሽፈት!!
ዶር ፈቃዱ ከፃፉት ይተወሰደ
የመደመር ፍልስፍናና የፍቅር ፖለቲካ መክሽፍ!!
ዶ/ር አቢይ የጠቅላይ ሚንስተርነትን ቦታ ሲይዙና ንግግር ሲያደርጉ ያልተደሰተ ኢትዮጵያዊ አልነበረም። በእኝህ „ብሩህና መልከ መልካምና ሳቂተኛ መሪ“ አገራችን ወደ አዲስ የታሪክ ምዕራፍ ትሸጋገራለች የሚል ዕምነት ነበረን። የዲሞክራሲውና አገርን በጋራ የመገንባት ዘመን መጣ ብለን አንዳንዶቻችን ሻንጣዎቻችንን ለማዘጋጀት ቀና ደፋ ስንል ነበር። በእርግጥም አብዛኛዎቻችን መንፈሳችን ከመነቃቃቱ የተነሳ የዛሬውና የመጭው ትውልድ አዲስ የተስፋ ብርሃን የሚያዩበት አገር የተቃረበ መስሎን ነበር። በዚህ ላይ የፍቅር መዝሙርና የመደመር ፍልስፍና ለአገራችን ግንባታ መመሪያ ይሆናሉ የሚል ዕምነት ነበረን። ይሁንና ግን ይህ ዐይነቱ ተስፋ ባጭር ጊዜ ውሰጥ ወደ ጨለማነት እየተሸጋገረ ይመጣል። ጊዜው የኛ ነው በማለት መዝናናት የጀመሩ ፅንፈኝ ኃይሎች ፍቅርንና መደመርን ከማሳየት ይልቅ መጤ እያሉ ማሳደድና መግደል፣ ወይም ደግሞ ከቤታቸው እንዲወጡ በማድረግ በየሜዳው ላይ እንዲወድቁ ለማድረግ በቁ። በመደመር ፈንታ መቀነስና መቀናነስ፣ በፍቅር ፈንታ ጥላቻና ማሳደድ ቦታውን ተኩ። በጠባብ መንፈስ የተወጠሩና የፍቅርንና የመደመርን ትርጉም መረዳት ያቃታቸው የዘመኑ ፅንፈኛ ኃይሎችና አንዳንድ የኦሮሞ ዲሞክራቲክ ግንባር ቀደም መሪዎች መዝናናትንና ማስፈራራትን ዋናው የአመራር ስልታቸው አደረጉ።
በመጀመሪያ መደመር የሚለው የፖለቲካ ዘይቤ ሳይንሳዊ ሳይሆን ሁሉንም ማግበስበስ ነው። „ፍልስፍናዉ“ በተግባር ሲመነዘር ብሩህ አመለካከትና ርዕይ ያላቸውን የተማሩ ዜጎችን መሰብሰቢያ ሳይሆን ቄሮዎችንና ኦነገዎችን ማግበስበሻ ዘዴ ለመሆን በቅቷል። በመደመር ስም ተግበስብሰው የገቡትና ቦታ የተሰጣቸው በቅናትና በጥላቻ መንፈስ ናላቸው የዞረና ስንትና ስንት ወንጀል የሰሩ ናቸው። አንዳንዶችም በውጭ ኃይሎች ደሞዝ እየተከፈላቸው በየሚኒስትሪው ውስጥ መቀመጫ የሚያሞቁ ናቸው። የአዲሱ የገዢ መደብ የማህበራዊ መሰረት ናቸው። በዚህ መልክ በመደመር ስም የፖለቲካ መድረኩ ለጽንፈኞች፣ ለሲአይኤና ለአረብ ተላላኪ ለሆኑት እንደነጃዋር ላሉት ሲለቀቅና እንደልባቸው እንዲፈነጩ ሲደረግ፣ ሰፊው ህዝባችን ደግሞ እንዲሸማቀቅ ተደርጓል። ባጭሩ የዶ/ር አቢይ አገዛዝ በመደመር ስም የፖለቲካ መድረኩን የሽወዳ ፖለቲካና የኦሮሞ ጽንፈኞች ማጠናከሪያ አድርጎታል ማለት ይቻላል። በዚህም መሰረት ይህንን አካሄድ የሚቃወሙ አይ ይታሰራሉ፤ ካሊያም በዘዴ እንዲወገዱ ይደረጋሉ። ሰሞኑን ወደ ውጭ የተለቀቀው የሺመልስ አብዲሳ ንግግር ይህንን ነው ያረጋገጠልን። አንደነ አቶ ታዬ ደንደዓን የመሳሰሉ የሺመልስ አብዲሳን አባባል ለማስተባበልና የፓርቲው የፖለቲካ ስልት እንዳልሆነ ለማረጋገጥ ሞክረዋል። እነ አቶ ታዬና ሌሎች ቀና አመለካከት አላቸው የሚባሉ „የኦሮሞ ፖለቲከኞች“ በሻሸመኔና በዝዋይ እንዲሁም በሌላ ቦታዎች እንደዚያ ዐይነት የዘገነነ ስራ ሲፈጸም ጣልቅ በመግባት ነገሩ እንዲበርድ አላደረጉም። ድርጊቱን አደባብሰው ነው ለማለፍ የሞከሩት። በአነጋገራቸውና በድርጊታቸው አንድን ማህበረሰብ ለማስተዳደር እንደማይችሉ ለማረጋገጥ ችለዋል። ኦሮሞ ነኝ ለሚለው ወጣትም ሆነ እዚያው ተወልዶ ላደገውና ከሌላ ብሄረሰብ ከተወለደው የትምህርትና የሙያ መሰልጠኛና የስራ ዕድል ማመቻቸት አልቻሉም። ወጣቱ በየሺሻው ቤት ተቀምጦ ጊዜውን የሚያሳልፍና ጨአት የሚቅምና፣ ሌላው ደግሞ በየመንገዱ ጊዜውን ዝም ብሎ የሚያሳልፍ ነበር፤ አሁንም ነው። እንደዚህ ዐይነቱን ምንም ህልም የሌለውንና ስራ-ፈቶ የተቀመጠን ወጣት ለመቀስቀስና ለመጥፎ ተግባር ለማሰማራት ደግሞ ቀላል ነው። እነ ጀዋርን በገንዘብ የሚደጉሙት የውጭ ኃይሎች፣ ግብጽ፣ ሳውዲ አረቢያና ሲአይኤ በዚህ መልክ ነው ጊዜን ጠብቀው አጠቃላይ ጦርነት ያወጁብን። እነ ሺመልስ አብዲሳና ግብረአበሮቹ ይህንን የመሰለውን የውጭ ሴራ ነው በቅጡ ያልተገነዘቡት። የመጨረሻ መጨረሻ እነውክለዋለን የሚሉትም ህዝብ ተጠቃሚ ሳይሆን በከፍተኛ ደረጃ እንደሚጠቃና ኃይሉም ሊበታተን እንደሚችል የገባቸው አይመስልም። በጣባብ አስተሳሰባቸው በመገፋፋት በአማራውና በተቀረው ብሄረሰብ፣ እንዲሁም በኦርቶዶክስ ሃይማኖት ተከታዮች ላይ ዘመቻ ሲከፍቱና ሲያሳድዷቸው በገንዘብ የናጠጡ እንደሳውዲ አረቢያ የመሳሰሉ አገሮችና የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም የውስጥ ለውስጥ አገርን የሚያፈራርስ ስራ እንደሚሰሩ ለመገንዘብ የቻሉ አይደሉም። ወደፊትም ሊገንዘቡ አይችሉም። ጭንቅላታቸው በዝቅተኛ ስሜት ስለተወጠረና ጥላቻን መመሪያቸው ስላደረጉ በጀመሩት የጥፋት ተግባር ከመግፋት ይልቅ የነገሩን ውስብስብነትና የውጭ ኃይሎችን ሴራ ቆም ብለው ለማጤን የሚችሉ ኃይሎች እንዳይደሉ አረጋግጠዋል። በሌላ ወገን ደግሞ እንደዚህ ዐይነት ዘግናኝ ድርጊት ከተፈጸመ በኋላ የፈለጉትን ቢዘላብዱም ከእንግዲህ ወዲያ ማንም የሚሰማቸውና የሚያምናቸውም የለም። ባለፉት ሁለት ዓመታትም ያረጋገጡት የራሳቸውን የበላይነት ለማስፈን ነው። በኦሮምያ ክልል የተካሄደውን ዘርና ሃይማኖት ተኮር ያደረገ ጭፍጨፋ ትላንት የተጀመረ ሳይሆን ባለፉት ሁለት ዓመታት ያየነውና እየተለማመድነው የመጣን ነን። ከሃጫሉ ሁንዴሳ ግድያና የቀብር ስርዓት በኋላ ዘርን የማጥፋትና ሀብትን የማውደም ዘመቻ ካለፈው የቀጠለና ከፍተኛውን ቦታ የያዘ ነው። በዚህ የዘር ማጥፋትና አገርንና ሀብትን የማውደም ዘመቻ ሁሉም ተጠያቂዎች ናቸው። ኢትዮጵያ ማንም እየተነሳ የሚፈነጭባት አገር ሳትሆን ብዙ መስዋዕትነት ተከፍሎባት ለእኛ የተላለፈች ነች። ኦሮሞዎች ብቻ አይደሉም ይህችን አገር የገነቡ፣ ወይም ደግሞ ብቻቸውን በመሆን ከውጭ የመጣን ጠላት የተጋፈጡት። ስለሆነም የኦሮሞ ልሂቃን በአውሮፓውያንና በአሜሪካን የኢቫንጄሊካን ሃይማኖት ቀስቃሽነትና ግፊት የሚያደርጉት ቅጥ ያጣ መራወጥና እነሱ ብቻ እንደተጨቆኑ አድርጎ ማቅረብ በህብረተሰብ ታሪክና ወይም በስልጣኔ ሚዛን የሚረጋገጥ አይደለም።
የኦሮሞ ሊህቃን ትረካና ይህንን ዐይነቱን ትረካ በተግባር የሚመነዝረው የዶ/ር አቢይ አገዛዝ ያልተገነዘቡት ነገር አለ። በመጀመሪያ ደረጃ አንዳቸውም ቢሆን የራሳቸውን የጎሳ አወቃቀር ስርዓትና የኢኮኖሚና የማህበራዊ መሰረት በፍጹም አያውቁም። ይሁንና ግን እየደጋገሙ ሊያሳምኑን የሚሞክሩት የአፄ ምኒልክ አገዛዝ ወደ ደቡቡ ክፍል ከመስፋፋቱ በፊት የዳበረና በሳይንስና በቴክኖሎጂ የሚገለጽ ማህበረሰብ እንደነበራቸው ነው። ትላልቅ ከተማዎች የነበሯቸውና፣ የኢኮኖሚና የንግድ እንቅስቃሴያቸውም ከፍተኛውን ቦታ የያዘ ነበር። በጥበብና በአርክቴክቸር፣ እንዲሁም በስነ-ጽሁፍ የላቅን ነበርን ይሉናል። በኢንፍራስትራክቸርም የተያያዙና በባቡርና የውስጥ ለውስጥ በሚካሄድ ተጓዥ የሚገናኙ ከተማዎች ነበረን ይላሉ። በስራ-ክፍፍልና በምርምርም ከሌላው ኢትዮጵያ ግዛት በልጠን የምንገኝ ነበርን ይሉናል። ይህንን ዐይነቱን ወርቅ የሆነና የዳበረ ስረዓት ነው በአፄ ምኒልክ የሚመራው ኋላ ቀር የአማራ ህዝብ መጥቶ ስልጣኔያችንን ያወደመብን እያሉ የተረት ተረታቸውን ይተርካሉ። በሌላ አነጋገር፣ የኦሮሞ ልሂቃን በቲዎሪና በኢምፔሪካል ደረጃ የማይረጋገጥ ነገር ነው የሚነግሩን። በሁለተኛ ደረጃ፣ እነዚህ ልሂቃን በአጠቃላይ ሲታይ አንድ ህብረ-ብሄር ሲመሰረት ስንትና ስንት መንገዶችን መጓዝ እንዳለበት ሊረዱ ያልቻሉ ናቸው። በሶስተኛ ደረጃ፣ አንድ ማህበረሰብ ወይም ህብረተሰብ በአንድ ጎሳ ብቻ አገርን ለመገንባት እንደማይችል የተረዱ አይደሉም፤ ለመገንዘብም አይፈልጉም። በህብረተሰብ ታሪክ ውስጥ በአንድ ጎሳና በአንድ ቋንቋ ላይ ብቻ የተመሰረተና የዳበረ፣ እንዲሁም የሳይንስና የቴክኖሎጂ ባለቤት የሆነ አገር በፍጹም የለም። በአራተኛ ደረጃ፣ አብዛኛዎቹ የእሮሞ ልሂቃን በውጭ ኃይሎች እየታገዙ ነው የሚንቀሳቀሱት። አስተማሪዎቻቸው የፕሮቴስታንት ሃይማኖት ተከታዮች ናቸው። እነዚህ ደግሞ ፋሽሽታዊ አመለካከት ያላቸው ናቸው። በጥቁር ህዝብ ዘንድ መከፋፈል እንዲኖርና ወንድማማች ህዝብ እርስ በእርሱ እንዲተላለቅ ሌት ተቀን የሚሰሩ ናቸው። እንደነ ጃዋር የመሳሰሉት ደግሞ በሳውዲ አረብያ፣ በግብጽና በአሜሪካኑ የስለላ ድርጅት የሚደገፉና የሚመከሩ ናቸው። እነዚህ ሁሉ ኃይሎች ናቸው በመደመር ስም አገር ቤት ተግበስብሰው በመግባት አገሪቱን ወደ ጦር አውድማነት የለወጧት። የሁለቱም ኃይሎች ዋና ዓላማ ከኢትዮጵያዊነት ጋር የተሳሰሩ ነገሮችን ማውደምና አዲስ የውጭ ኃይሎች ተቀጥያ የሆነች አገር መመስረት ነው። እነጃዋር ደግሞ የእስላሚክ ሪፑብሊክን ማቋቋም ነው። የዶ/ር አቢይ አገዛዝ አውቆም ሆነ ሳያውቅ ይህንን ነው ያዘጋጀልን።
ለማንኛውም አገዛዙም ሆነ እነዚህ ኃይሎች ያልገባቸው አንድ ነገር አለ። በእነሱ አካሄድና ቅስቀሳ የፈለጉትን ግብ መምታት እንደማይችሉ ነው። ምናልባት ዋና ዓላማቸው አገርን ወደ ጦር አውድማነት መለወጥ ባይሆንም ድርጊታቸውና ቅስቀሳቸው ሁሉ የውጭ ኃይሎችን በመጋበዝ የኢራክ፣ የሶርያ፣ የሊቢያና የአፍጋኒስታን ዐይነት ሁኔታ መፍጠር ነው። የሰሜን አትላንቲክ ጦርም (NATO) ይህንን ይነቱን የግብዣ ሁኔታ ነው የሚጠባበቀው። ይህ ማለት ምን ማለት ነው? የዛሬው የገዢ መደብና ሌሎች የኦሮሞ ጽንፈኞች የዓለም ፖለቲካ እንዴት እንደሚካሄድ አልገባቸውም። የእኛው መፋጠጥና የእርስ በእርስ መጨራረስ ለእነሱ የስርግ ምላሽ እንደሆነ የተገነዘቡ አይደሉም። አንድ አገር በጠንካራ ዕይታና ውስጣዊ አንድነት ብቻ እንደሚገነባ የተረዱ አይመስሉም። ከቻይና፣ ከራሺያና፣ ከሲንጋፖርና ከጃፓን የተማሩት ነገር የለም። ጥረታቸውና ትግላቸው በሙሉ በደመ-ነፍስ በመመራት የኢትዮጵያን መፈረካከስ ማፋጠን ነው። ግፉበት እንላቸዋለን!! በርቱ በርቱ እንላቸዋለን!! ይሁንና ግን በዚህ ድርጊታቸው ገነት ውስጥ ሳይሆን ገሃነም ውስጥ እንደገሚገቡ ልናረጋግጥላቸው እንችላለን!!
ባጠቃላይ ሲታይ ዶ/ር አቢይ ስልጣንን ከተቆናጠጡ ጀመረው በአገሪቱ ውስጥ ስላም እንዲሰፍን ያደረጉት ምንም ዐይነት ዕርምጃ የለም። የዶክትሬት ስራቸው ሰላምና መታረቅ (Peace and Reconciliation) የሚል ቢሆንም ድርጊታቸው በሙሉ የኦሮሞ በላይነትን ማስፈን ነው። አቶ ሺመልስ አብዲሳም የነገረን ይህንን ነው። የብልጽግና ፓርቲ ዋና ዓላማው አዲስና ዲሞክራሲያዊት ኢትዮጵያን መገንባት ሳይሆን የኦሮሞ የበላይነትን ማስፈንና አዲስ የታሪክ አሻራ ማስፈር ነው። የአዲስ አበባን ዲሞግራፊ መለወጥና ስሟንም ወደ ፍንፍኔ የመለወጡ ጉዳይ የስትራቴጂው ዋናው አካል ነው። ለዚህ ደግሞ የአዲስ አበባው ምክትል ከንቲባ ታከለ ዑማ የቤት ስራውን ሰርቷል። ባጭሩ ታሪክ እንደዚህ ነው። አሁን ትግሉ የለየለት ነው። እኛ ሳንናገር ምን እንደሚፈልጉና ዓላማቸውም ምን እንደሆነ በዝርዝር ነግረውናል። በሌላ ወገን ግን የሺመልስ አብዲሳ አስተማሪ የሆኑት ዶ/ር ዳኛቸው እንደነገሩን ከሆነ ሺመልስ አብዲሳ ፍልስፍና የተማረና፣ በተለይም የፕላቶንን ሪፑብሊክ መጽሀፍ እንዳነበበና ለከፍተኛ ሹመትም እንደሚበቃ ነው። ይሁንና ግን ፕላቶ ሪፑብሊክ በሚለው መጽሀፉ ውስጥ የሚያስተምረን ስለፍትሃዊነት፣ አንድን ከተማ ወይም አገርን በስነ-ስረዓትና ጥበባዊ በሆነ መልክ መገንባትና ማስተዳደር፥ እንዲሁም በገዢው መደብና በተገዢዎች መሀከል መቃቀር እንዳይኖር አንድን ከተማም ሆነ አገርን የሚያስተዳድሩ ሰዎች ምን ዐይነት ፖለቲካ መከተል እንዳለባቸው ነው። ከዚህም አልፎ ፕላቶ በመጽሀፉ ውስጥ ስለ ስራ-ክፍፍልና ስለንግድ አስፈላጊነት በማውሳት በዚህ አማካይነት በአንድ አገርም ሆነ በአንድ ከተማ ውስጥ በሚኖር ህዝብ መሀከል ውስጣዊ ግኑኝነት(Organic Link) ይፈጠራል። በመቀጠልም በፕላቶንም ሆነ የሱን ፈለግ በመከተል የፖለቲካ ፍልስፍናን ባስተማሩት ጠቢባን መሰረት ተፈጥሮም ህብረተሰብ ልዩ ልዩ ነገሮች የሚገለጽባቸው፣ እዚያው በዚያው አንድነትና ብዝሃት የሚታዩባቸው ናቸው። በሌላ አነጋገር ተፈጥሮም ሆነ አንድ ህብረተሰብ አንድ ወጥና አንድ ዐይነት አመለካከት ባላቸው ነገሮች በፍጹም አይመሰረቱም። ይህ የተፈጥሮና የህብረተሰብ ህግ ነው። ከዚህም በላይ በፕላቶ ዕምነት በአንድ አገር ውስጥ የሚፈጠር ቀውስ ዋናው ምክንያቱ ኢ-ፍትሃዊነት ሲነግስና ስልጣንን የጨበጡ ኃይሎች ከጥበባዊ ፖለቲካ ይልቅ ሲባልጉና፣ በትዕቢትና በደመ-ነፍስ አገርን መምራት ሲጀምሩ ነው። ፖለቲካን ከሞራል ጋር ማገናኘት ሲሳናቸውና ከሀቀኛነት ይልቅ ማታለልን ዋናው የፖለቲካቸው ዘይቤ ሲያደርጉ በአንድ አገር ውስጥ ያልታቀደ ብጥብጥ ወይም የእርስ በእርስ ጦርነት እንዲከሰት መንገዱን ያሳምራሉ። ስለሆነም የፕላቶ ዋናው የፖለቲካ መመሪያ ፍልስፍናዊ አርቆ ማሰብ ነው። አንድ መሪ ራሱን ወደ ውስጥ የመመልከትና በየጊዜውም የመመርመር ኃይል እንዲኖረው ያሳስባል። በእሱ ዕምነትም በጎሳ ላይ የተመሰረት ፖለቲካ ፖለቲካ ሳይሆን የብጥብጥ መነሻ ነው። ስለሆነም እያንዳንዱ ሰው እራሱን እንደነፃ ሰው አድርጎ መቁጠርናና፣ እንዲሁም የጠቅላላው የማህበረሰብ አካል መሆኑን መገንዘብ ያለበት እንጂ ከዚኸኛው ወይም ከዚያኛው ብሄረሰብ የመጣሁ ነኝ ብሎ ማሰብ የለበትም። ይህ ሲሆን ብቻ ማንኛውም ሰው ሰው መሆኑና በእግዚአብሄርም አምሳል እንደተፈጠረ ይገነዘባል። ይሁንና በፕላቶን ፍልስፍና የተመረቀው ሺመልስ አብዲሳ የሚነግረንና ተግባራዊም የሚያደርገው ፖለቲካ ሌላ ነገር ነው። ፕላቶንም ይህንን የሺመልስ አብዲሳን ንግግር ከመቃብሩ ውስጥ ሆኖ ቢሰማ ኖሮ ይገላበጥ ነበር።
ይህን ካልኩኝ በኋላ አንዳንድ አገዛዙን የሚደግፉ፣ በተለይም ለዶ/ር አቢይ ልዩ ፍቅር ያላቸው በአገራችን ምድር የተካሄደውን ዘርና ሃይማኖት ተኮር ጭፍጨፋ ጂኖሳይድ አይደለም፣ ዘር ተኮርም ሊባል አይገባውም፣ ወይም አትበሉ ለሚሉት የምነግራቸው ነገር ማፈር አለባቹሁ፤ ከእንግዲህ ወዲያም እንደሰው አንቆጥራችሁም ነው የምላቸው። አቶ ኦባንግ ሜቶ በትክክል እንዳለው ኢትዮጵያ ውስጥ የተደረገውን ጭፍጨፋ ጄኖሳይድ ብላችሁ አትጥሩ ማለት ከሰው በታች እንደመውረድ የሚቆጠር ነው። ይህንን የሚሉ ሰዎች መንፈሰ-አልባ ናችው። ፍቅራቸው ለኢትዮጵያ ህዝብ ሳይሆን ለአንድ ግለሰብ ብቻ መሆኑን ነው ያረጋገጡት። ምናልባት በዚህ አስተሳሰባቸው ፖለቲካ የሰሩ መስሏቸው ይሆናል። ተሳስተዋል። ፖለቲካና ሞራል፣ ፖለቲካና ሀቀኝነት፣ ወይም ለዕውነት መቆም አንድ ላይ ሊሄዱ አይችሉም ያለው ማነው? በፖለቲካ ቲዎሪና ፍልስፍና መሰረት ሰውን ስትገድልና ስታሳድድ ወይም ስቃዩን ስታሳየው ብቻ ነው ፖለቲካ የሚባለው ነገር ሳይንስነቱ ሊረጋገጥ የሚችለው ያለው ማንነው? በአንድ አገር ውስጥ እንደዚህ ዐይነት አሰቃቂ ድርጊት ሲፈጸም የአንድ ጠቅላይ ሚኒስተር ዋና ተግባር ዝም ብሎ መመልከት ብቻ ነው ያለውስ ማን ነው?
ያም ሆነ ይህ ዶ/ር አቢይ ስልጣን ላይ ከወጡ ጀምሮ በአገራችን ምድር የህዝቡን ኑሮ የሚያሻሽልና እርግጠኝነትም እንዲሰማው የሚያደርገው ነገር ተግባራዊ ሲሆን አይታይም። ሰፊው ህዝብ የመደራጀትና የመታጠቅ መብት፣ እንዲሁም የመጠየቅ መብት የለውም። ያልተማረና ያልነቃ እንዲሁም ያልተደራጀ ህዝብ ደግሞ በቀላሉ በውጭ ጠላት ሰለባ ይሆናል። አርቆ የማሰብ ኃይሉም ደካማ ስለሚሆን መንግስትም ሆነ የውጭ ኃይሎች የሚነግሩትን ብቻ በመስማት አገርና ባህል እንዲፈራርሱ ያደርጋል። ዶ/ር አቢይም እንዲዚህ ዐይነቱን ዝም ብሎ የሚሰማቸውን ዜጋ ወይም ሰው የሚፈልጉ ነው የሚመስለው። ስለሆነም የምጠየቅና የምተች አይደለሁም ባይ ናቸው። እኔ የምለውን ዝም ብላችሁ ስሙ ነው የሚሉን። የሳቸውን ዕምነት የሚያራምዱና በየኤምባሲዎች በመጋበዝ መጽሀፍ ቅዱስን የሚያነቡ የሚነግሩንም ይህንን ነው። መንግስትን አትጠይቁ፣ አትተቹ ይሉናል። የእናነተ ዋና ተግባር እንደከብት ዝም ብላችሁ መነዳት ነው። በዚህ አነጋገራቸው እነካንትና ሄገል፣ እንዲሁም በሺሆች የሚቆጠሩ የኢንላይተንሜንት ምሁራን ያስተማሩንንና የተዋጉትን ዲስፖታዊ አመለካከትና አገዛዝ ትክክል አይደለም ነው የሚሉን። ስለሆነም ቄሮዎች ሲደበድቧችሁና ሊገድሏችሁ ሲመጡ ዝም ብላችሁ እጃችሁን ስጡ የሚል ፍልስፍና ነው የሚያስፋፉት። አገዛዙን መቃውም ወይም መተቸ ክልክል ነው። አትተቹ፣ አትተንፍሱ እየተባልን ነው። በሌላ ወገን ደግሞ መጽሀፍ ቅዱሱ የሚለን፣ ፈልግ ታገኛለህ፣ ጥያቄም ጠይቅ መልስ ይሰጥሃል፤ በመጠየቅና በመመራመር ብቻ አዲስ ነገር ታገኛለህ፤ አንኳኳ በሩ ይከፈትልሃል፤ ለማየት ዐይን ሰጥቼሃለሁ፤ ለማሰብም አዕምሮ ለግሼአለሁ፤ ስለሆነም ዝምብለህ እንደ ከብት አትነዳ ነው የሚለን። በማሰብና በመመራመር ኃይልህ የተፈጥሮን ምስጢር በማወቅ አዲስና የተሻለ ማህበረሰብ በመገንባት ተስማምተህ ኑር። ጭንቅላትህን የማትጠቀምና አርቀህ የማታስብ ከሆነ ግን ለዝንተ-ዓለም እንደተረገምክ ትኖራለህ ይለናል።
ስለሆነም የዛሬውን የአገራችንን ሁኔታ በምንቃኝበት ጊዜ አገራችን በለውጥ ስም ወደ ዲስፖታዊ አገዛዝ እያመራች ነው። ወደ ኦሮምያ ክልል ስንመጣ ደግሞ ፋሺሽታዊ አገዛዝ የሚመስል የሰፈነባት ነው። የክልሉን የተለያዩ ከተማዎችም ሆነ ገጠሩን ያለሙና የገነቡ፣ የቅድመ-አያቶቻቸው ያቀኗቸውና ከሶስት መቶና አራት መቶ ዐመት በፊት የመሰረቷቸውን መንደሮችና ከተማዎች የልጅ ልጅ ልጆቻቸው መጤዎች እየተባሉ ይባረራሉ፤ አሊያም ይገደላሉ፤ የተቀሩት ደግሞ ፍዳቸውን ያያሉ። በዛሬው ወቅት የእሮሚያን ክልል የሚያስተዳድሩት መሪዎችና ቄሮዎች ለማሳመን የሚሞክሩት መሬቱንና በመሬት ውስጥ የሚገኘውን ሁሉ እኛ ነን የፈጠርነው፣ አሊያም ደግሞ እግዚአብሄር ለእኛ ብቻ ባርኮ የሰጠን መኖሪያ ነው እያሉ የሚነግሩን። ባጭሩ ፀረ-ስልጣኔና አገር በታታኝ የሆነ አገዛዝ መጤ የሚባለውን፣ ግን ደግሞ እዚያው የተወለደውንና ያደገውን፣ እንዲሁም ሀብት ያፈራውን እያዋከበና በፍርሃት እንዲኖር አድርገውታል። ይህ ዐይነቱ አገዛዝ በ21ኛው ክፍለ-ዘመን መኖር የለበትም።
ወደ ፌዴራል አስተዳደሩ ስንመጣ ደግሞ በመንግስት መኪና ውስጥ አሁንም ቢሆን ስንትና ስንት ወንጀለኞች ተሰግስገዋል። ከወያኔ ጋር እጅና ጓንቲ ሆነው ሲሰሩ የነበሩ አዲስ ሹመት ተስጥቷቸው አሁንም ቢሆን ፀረ-ዲሞክራሲ ስራቸውን ይሰራሉ። የመንግስቱ መኪና ባልተገለጸላቸውና አደገኛ በሆኑ ሰዎች የተሰገሰገ ነው። ስለሆነም በፖለቲካው መስክ ምንም ዐይነት ለውጥ አልተካሄደም። ወደ ኢኮኖሚ ፖሊሲው ስንመጣም የዶ/ር አቢይ አገዛዝ አሁንም ቢሆን የወያኔ አገዛዝ ያራምድ የነበረውን የኒው-ሊበራል የኢኮኖሚ ፖሊሲ ነው ተግባራዊ የሚያደርገው። የኢኮኖሚ ፖሊሲ ነዳፊዎችም በዓለም ባንክ የተቀመጡና በእሱና በዓለም አቀፍ የገንዘብ ድርጅት የሚታዘዙ ናቸው። የኢትዮጵያን ህዝብ ጥቅም የሚያስቀድሙና ኢኮኖሚውም በሳይንስና በቴክኖሎጂ ተመስርቶ እንዲንቀሳቀስ የሚያደርጉ ሳይሆን ዋና ዓላማቸው አገራችን በዓለም አቀፍ የፋይናንስ ኦሊጋሪክ ስር እንድተወድቅና በኢንቬስትሜንት ስም እንድትቸበቸቭ ማድረግ ነው። ሞራላዊ ብቃትና ታሪካዊ ኃላፊነት የማይሰማችው ናቸው። የአገር ወዳድነትና የብሄራዊ ስሜት የሌላቸው ናቸው። ከዚህም በላይ የዎል ስትሪት ታዛዢዎችና የኧርንስት ያንግ ተጠሪዎች በአማካሪነት በመስራት የአገር ሀብት እንዲሸበሸብ እያደረጉ ናቸው። በመዋዕለ-ነዋይ ስም አገሪቱ ወደ ተራ ሸቀጣ-ሸቀጥነት እየተለወጠችና ህዝባችንም ብሄራዊ ነፃነቱ እየተገፈፈ ነው። የኢኮኖሚ ፖሊሲውን የሚያረቁና ከነፃ ገበያ ገበያ በስተቀር ሌላ አማራጭ የለም ብለው የሚነግሩን ሰዎች ካፒታሊዝም በምን ዐይነት ሎጂክና ህግ እንደተገነባ የሚያውቁ አይመስለኝም። በእነሱ ዐምነት አንድ ዐይነት የኢኮኖሚ ፖሊሲ ብቻ ነው በኢኮኖሚ ፖሊሲና በአገር ግንባታ ታሪክ ውስጥ ያለውና ለዘለዓለምም የሚኖረው። ይኸውም ኒዎ-ሊበራሊዝም ነው።
ከአጠቃላዩ የአገራችን ሁኔታ ስንነሳ በፖለቲካውም ሆነ በኢኮኖሚው መስክ፣ በማህበራዊም ሆነ በአጠቃላይ የአገር ግንባታ አገራችን ለውጥ የሚካሄድባት አገር አይደለችም። ለለውጥና ለአገር ግንባታ መሰረታዊ የሆነው የሰላምና የፀጥታ ጉዳይ የሚተገበርባት አገር አይደለችም። ከዘጠና በመቶ በላይ የሚሆነው ህዝብ በታጠቁና የመንግስትን መኪና በተቆናጠጡ ሰዎች በፍርሃት የሚኖርባትና ፍዳውን የሚያይባት አገር ሆናለች። የመንግስት መኪና ከተጨቋኝ ባህርይው እስካልተላቀቀና ህዝቡም በማንኛውም መስክ የመሳተፍና ሃሳቡን የመግለጽ፣ እንዲሁም የመጠይቅና የመተቸት፣ ሰላማዊ ሰልፍም የማድረግ መብት እስከሌለው ድረስ ስለ ብልጽግና ማውራት በፍጹም አይቻልም። ከዘጠና በመቶ በላይ የሚሆነው ህዝብ በተገለለበት አገርና መንግስት የሚባለው ፍጡር ከአገር ጥቅም ይልቅ የውጭ ኃይሎችን ጥቅምና ፍላጎት በሚያስቀድምበት አገር ብልጽግና እያሉ መወትወት ትልቅ የታሪክ ወንጀል እንደመስራት ይቆጠራል። አንዳንድ ጋዜጠኞች ነን ብለው ራሳቸውን የሚጠሩ ግለሰቦችና የቴለቪዥን ጣቢያዎች የዛሬውን አገዛዝና በአገዛዙ ዙሪያ የተሰበሰቡትን የለውጥ ኃይሎች እያሉ መጥራታቸ ከፍተኛ የታሪክ ወንጀል እንደሰሩ ያስቆጥራቸዋል። ስለሆነም በእናት ኢትዮጵያ ስም የምንለምናቸው ክሪቲካል የሆኑ መጽሀፎችን እንዲያነቡና አገሮች እንዴት እንደተገነቡና፣ ደሃ ወይም ኋላ-ቀሩ የሚባሉ አገሮች በምን ምክንያት ኋላ እንደቀሩ እንዲማሩ ነው። ችግር ካለባቸው የሊትሬቸር ዝርዝር ልናቀርብላቸው እንችላለን። ልናስተምራቸውም ዝግጁ ነን። ለመማርና ሀቁን ለማወቅ አንፈልግም የሚሉ ከሆነ ደግሞ የምንለምናቸው ዝምብላችሁ ተቀመጡ ነው። ሰውን አታሳስቱ እንላቸዋለን። ካለበለዚያ ገሀነመ-እሳት ትገባላችሁ እንላቸዋለን።
መደምደሚያ!
ዛሬ አገራችን በዚህ ሁኔታ ውስጥ ለመውደቅ የቻለችው በዛሬው አገዛዝ የግንዛቤ እጦት ብቻ አይደለም። ለዛሬው ሁኔታ መፈጠር የተለያዩ ኃይሎች በማወቅም ሆነ ባለማወቅ ተሳትፈዋል። አፄ ኃይለስላሴ ባለማወቅ ተግባራዊ ያደረጉት የኢኮኖሚና የትምህርት ፖሊሲ ብሄራዊ ባህርይና በራሱና በህዝቡ ላይ የሚተማመን ዜጋ ብቅ እንዳይልና የታሪክን አደራ እንዳይሸከም አድርጎታል። በአፄው ዘመን የተካሄደው ፖለቲካ ፊዩዳላዊና የሰፊውን ህዝብ አስተሳሰብ ቆልፎ የሚይዝ ነበር። አብዮቱ ከፈነዳ በኋላ የኢትዮጵያ ህዝብ አዲስ የታሪክ ምዕራፍ ለመስራት ዕድል ቢያገኝም ስልጣን ለመያዝና ፋሺሽታዊ አገዛዝን ለማስፈን በፈለጉ የግራና የቀኝ ኃይሎች ህልሙ ሊጨናገፍ ችሏል። ከዚህም በላይ በሲአይኤ የተመለመሉና፣ ለኢትዮጵያ ህዝብ አሽከር ከመሆንና ታሪክን ከመስራት ይልቅ ለአሜሪካን አገልጋይ መሆንን የመረጡ ኃይሎች የአብዮቱ ፍሬ እንዲቀለበስ አድርገዋል። ከሲአይኤ በሚጎርፍላቸው ዕርዳታ በአገራችንና በህዝባችን ላይ ጦርነት አውጀዋል። በአጠቃላይ ሲታይ አገራችን እንደዚህ ዐይነት ፈተና ውስጥ ልትወድቅ የቻለችው በውስጥ ኃሎች ነው። ህውሃትና ሻቢያ፣ ኦነግና ሌሎች የነፃ አውጭ ድርጅቶች፣ ኢህአፓና ኢድህ… ወዘተ. እነዚህ ሁሉ ከዚያች ምስኪን አገር የተወለዱና አገሪቱን ፍዳዋን እንድታይ ለማድረግ የበቁ ናቸው። በተጨማሪም ዛሬ አገራችን እየፈራረሰች ነው ብለው የሚጮሁና ለአንድ ኢትዮጵያ እንታገላለን የሚሉ አንዳንድ ሻለቃዎችና ጄኔራሎች፣ እንዲሁም የደጃዝማች ልጆች የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም የጥፋት ተላላኪ በመሆን በህዝባችንና በአገራችን ላይ ጦርነት አውጀው እንደነበርና ዛሬም የጥፋት ተልዕኮአቸውን እያሟሉ እንደሆነ ግልጽ ነው። ዋና ዓላማቸውም ስልጣን ላይ ቁጥጥ በማለት የአሜሪካንን ተልዕኮ ለማሟላት እንጂ አዲስና የጠነከረች፣ እንዲሁም ዲሞክራትክ ኢትዮጵያን ለመገንባት አይደለም።
የእነዚህ የውስጥ ኃይሎች ችግር ግልጽ ነው። ህልማቸው ስልጣኔና ማምጣት ሳይሆን ስልጣን መያዝ ብቻ ነው። የዚህ ዐይነቱ ጭፍን አስተሳሰብና የሴራ ሰለባ መሆን ዋናው ምክንያት የዕውቀት ማነስና ጭንቅላታቸው ባለመዳበሩ ነው። አዕምሮአቸው በሰብአዊነት መርሆ ላይ በተመሰረተ ዕውቀት ያልተገነባ በመሆኑ ሀቀኛውን ከአሳሳቹ የመለየት ኃይል የላቸውም። ድርጊታቸውንም ለመመርመርና ጥፋታቸውንም ለማረም የሚችሉ አይደሉም። አብዛኛዎቹ ድርጅቶችና ግለሰቦች ሰለሳና አርባ ዓመት ያህል ታግለናል ቢሉም በሂደት ውስጥ ምንም የተማሩት ነገር የለም። መንፈሳዊ ተሃድሶንና ነፃነትን የተቀዳጁ አይደሉም። በ21ኛው ክፍለ-ዘመን እየኖሩ ለማድመጥና ለመማር የሚፈልጉ አይደሉም። የችኮነት ባህርይ የሚያጠቃቸው ናቸው። ራሳቸውን መመልከት የማይችሉና የታሪክን ሂደት ያልተገነዘቡ ናቸው። በፈጸሙት የታሪክ ወንጀል የሚዝናኑ ናቸው። ትላንትም ሆነ ዛሬ ድርጊታቸው በሙሉ ሳይንስንና ፍልስፍናን እንዲሁም ቲዎሪን የሚፃረር ነው። ምንም ዐይነት ፍልስፍናዊ መመሪያ የላቸውም። ከዚህ ሁኔታ ስንነሳ የአገራችን ሁኔታ በጣም አሳሳቢና ህዝባችንም ካለአንዳች መሪ ብቻውን የቀረ ነው። ስለሆነም ጥያቄያችን ከዚህ አሳሳቢ ሁኔታ እንዴት እንውጣ? የሚል ነው። መጮኽና ድረሱልኝ ማለት የሚያዋጡ የትግል ስትራቴጄዎች አይደሉም። አንድ ህዝብ ነፃ ሊወጣ የሚችለውና የሳይንስና የቴክኖሎጂ ባለቤት ሊሆን የሚችለው በራሱ ጥረትና ኃይል ብቻ ነው። ለዚህ ደግሞ ኃይልን መሰብሰብና በጠራ ፍልስፍና ዙሪያ ትግል ማድረግ ያስፈልጋል። በፉከራና በዛቻ አንድ አገር ነፃ ልትወጣ አትችልም። አንድ አገር ነፃ ሊወጣ የሚችለው በምሁራዊ ኃይልና በምሁራዊ እንቅስቃሴ ዙሪያ ብቻ ነው። የጠብመንጃ ትግል ፀረ-ሳይንስና ፀረ-ስልጣኔ ነው። ኃይል ጨራሽና የአንድን አገር ሁኔታ የባሰውኑ ውስብስብ የሚያደርግ ነው። ስለሆነም መደረግ ያለበት ትግል ሳይንሳዊና ፍልስፍናዊ መሆን አለበት። በአገዛዙም ላይ ዕውነተኛ ጫና ማድረግ የምንችለው በዕውቀት ዙሪያ የተሰባሰብንና በጠራ ዕውቀት አማካይነት ትግልና ግፊት ስናደርግ ብቻ ነው። ይሁንና ግን በኢትዮጵያ ስም እዚህና እዚያ ባንዲራ አንግበው የሚታገሉና፣ በተለይም በአሁኑ ወቅት በአማራው ላይ ጦርነት ተከፍቶበታል ብለው ድምጻቸውን የሚያሰሙ- ነገሩ ሀቅን ያዘለ ቢሆንም- አንዳንድ ግለሰቦችና ድርጅቶች ሳይንሳዊና ፍልስፍናዊ ግንዛቤያቸው በጣም ደካማ ነው። እናካሂዳለን የሚሉት ትግል በፍልስፍና፣ በሳይንስና በቲዎሪ፣ በፖለቲካ ሳይንስና በሶስዮሎጂ፣ እንዲሁም በልዩ ልዩ የኢኮኖሚ ቲዎሪዎች ላይ ተመስርቶ የሚካሄድ ትግል አይደለም። አስተሳሰባቸው ይበልጥ ፊዩዳላዊ እንጂ ከበርቴያዊ ወይንም የሊበራል አስተሳሰብን ያዘለና የተገለጸለት አይደለም። ስለሆነም ታሪክን የሚረዱት ቆሞ እንደሚቀር እንጂ ሂደታዊ እንደሆነና በሂደት ውስጥ በአንድ ህብረተሰብ ውስጥ ሊበላሹም ሆነ ሊታደሱ የሚችሉ ነገሮች እንደሚኖሩና የኃይል አሰላለፍ ለውጥም እንደሚካሄድ አይደለም። ስለሆነም ትግላቸው ንቃተ-ህሊናን የተላበሰና ለፖለቲካ ዲስኮርስና የአንድን ህብረተሰብ ችግር ተረድቶ መፍትሄ ለመፈለግ የሚያስችል አይደለም። ባጭሩ ትግላቸውና አገላለጻቸው ዘመናዊነት የሌለው ወይም ደግሞ ያልተገለጸለት ነው ብሎ አፍን ሞልቶ መናገር ይቻላል። ከዚህ ዐይነቱ አስተሳሰብ እስካልተላቀቅን ድረስ የአገራችንን የተወሳሰቡ ችግሮች ለመረዳትና መፍትሄም ለመፈለግ በጣም ያስቸግራል።
በሌላ ወገን ደግሞ በዶ/ር አቢይ አህመድ የሚመራው አገዛዝ ሊገነዘበው የሚገባው መሰረታዊ ነገር አለ። አንድን አገር በሽወዳና በተንኮል መምራት በፍጹም አይቻልም። ወደ ተፈለገው ግብም አያደርስም። በግልጽ እንደሚታየው የውጭ ጠላቶቻችን፣ ከግብጽ እስከሱዳን፣ ከሳውዲ አረቢያ እስከተቀሩት የአረብ አገሮችና አሜሪካና የተቀሩት የምዕራብ አውሮፓ አገሮች ሌላ ዐይነት የሩዋንዳ ዐይነት ዕልቂት በአገራችን ምድር እንዲታይ ይፈልጋሉ። ከዚያም በኋላ አገራችንን እንደዩጎዝላቢያ ለመሰነጣጠቅና የተዳከሙና በቀላሉ ሊታዘዙ የሚችሉ ትናንሽ አገሮችን ማየት ይፈልጋሉ። አሜሪካንና የተቀረው የምዕራብ አውሮፓ አገሮች ከጎናችን ይቆማሉ ማለት የዋህነትና የዓለምን የፖለቲካና የሚሊታሪ ኃይል አሰላለፍ አለማወቅ ነው። ስለሆነም አገዛዙ ስትራቴጂካሊ ማሰብ አለበት። ኃይልን የሚበታትንና አገር ወዳድ ኃይሎችን የሚያጠቃ ፖለቲካ ማካሄድ የለበትም። በዚህ ዐይነት ፖለቲካ የመጨረሻ መጨረሻ ጠቅላላው የኢትዮጵያ ህዝብ ነው የሚጠቃው። ስለሆነም ስትራቴጂካሊና አርቆ ማሰብ የፖለቲካ ዋናው ጥበብ መሆን አለባቸው። መልካም ግንዛቤ!!