(courtesy: Tesfaye Gebreab)
የጃዋር የግድያ ሙከራ!
=================
የ
ESAT ጋዜጠኞች በትናንት ዝግጅታቸው እንዲህ አሉ፣
ጃዋር ለኦሮሞ ህዝብ አንድ የውሃ ጉድጉዋድ እንኩዋ አልቆፈረም! አንድ ዳቦ አልቸረም። እሱ በምቾት ምርጥ ምርጡን እየበላ የኦሮሞ ህዝብ. . .
እንዲህ ብለው ሲያለቃቅሱ ሰማሁ። በተያያዘ የኦሮሞ ወጣት ጃዋርን እንዳይሰማ፣ እንዳይከተል ደጋግመው ሲለምኑም አዳመጥኩ።
አንድ እውነት አለ።
ጃዋር ለኦሮሞ ህዝብ ዳቦ አልሰጠም።
ምን ለማለት ነው? የኦሮሞ ህዝብ እንኩዋን ለራሱ ለጎረቤቶቹ ዳቦ ሆኖ የኖረ ህዝብ አይደለም እንዴ?
አንድ ነጥብ ላንሳ!
ለሰው ልጅ ከምንም ነገር በፊት ክብሩ ይበልጥበታል። በዚህ ቀመር ጃዋር ለኦሮሞ ክብር ነው። አጀንዳችን ክብር እንጂ ዳቦ አይደለም። ስለሆነም የኦሮሞ ወጣት የጃዋርን ቃል እየሰማ ህይወቱን በፈቃዱ ሲሰጥ እያየን ነው። የኦሮሞ ወጣት ጃዋርን የሚሰማው ለመጪው ዘመን ዳቦ ሳይሆን ለመጪው ዘመን የኦሮሞነት ክብር እና ኦሮሙማ ነው። ቄሮ/ቀሬ ህይወቱን የሰጠው ለዳቦ ሳይሆን ለማንነቱ ክብር ነው። ወተት እና ቅቤ መች አጀንዳ ሆኖ ያውቅና! የኦሮሞ ፈረሶች ምሳቸውን ገብስ እና ዝርግ ጎመን በሚበሉበት አገር ESAT ስለ ምግብ እያነሳ ኦሮሞን ሊቀሰቅስ ይሞክራል!?
ጃዋር የሰው ተፈጥሮ እንደሌለው ጨካኝ ሲሳል ሰነበተ። ይኸው ሆነ ችሎታችን? በርግጥ ጃዋርን ሰይጣናዊ ፍጡር አድርጎ መሳል ለኢትዮጵያ አንድነት ጠቃሚ ሆኖ ተገኘ? በልምድ የወረሳችሁት ስም የማጠልሽት ባህርይ በርግጥ በዚህ ዘመን ኢትዮጵያውያን አብረው ይኖሩ ዘንድ ያግዛል? አባባላችሁስ እውነት ነው? ወይስ መንጋ ዘመቻ! መንጋ ፕሮፓጋንዳ!
ከመነሻው የESAT ጋዜጠኞች የኦሮሞን ህዝብ የት ያውቁታል? ትናንት፣ ከትናንት ወዲያ "መንጋ" እያሉ በአሽሙር ሲያላግጡበት አልነበረም? ዛሬ እንዴት ጆሮ እንዲሰጣቸው ይጠብቃሉ? እና የሰው ልጅ ለክብሩ ሲል ምንም ነገር ሊያደርግ ይችላል። ከሚሰድቡት ጋር አብሮ ከመኖር ነጻነቱን ሊያውጅ ይችላል። ተቆጥቶ አገር ሊያቃጥል ይችላል። በደምፍላት ነፍስ ሊያጠፋ ይችላል። በታሪክ የታየ ነው። በፈረንሳይ እና በሩስያ አብዮቶች ታይቶአል። ምን ሩቅ አስኬደን? በኢትዮጵያም ታይቶአል።
መንግስቱ ሃይለማርያም ፊውዳሎቹ ላይ የፈጸመው መራራ የግድያ ድርጊት ስነልቦናዊ መነሻው ገና አልተጻፈም። አጤ
ቴዎድሮስ በተለይ የሸዋ መኩዋንንት ላይ የጨከነበት ምክንያቱ በትክክል አልተነገረም።
እና የሰው ልጅ በዳቦ ብቻ አይኖርም። ከዳቦ በፊት ክብሩን ሊመርጥ ይችላል። አንድን ሰው ብትመታው የመርሳት እድሉ ሰፊ ነው። አባቱን ወይም ልጁን ገድለህበትም ይታረቅሃል። ክብሩን ከነካኸው ግን ሮሮ ደረጃ ላይ ይደርሳል። ክብሩን ከነካህበት መቸም አይረሳውም። መቸም አይታረቅህም። አንተ ብትረሳ እሱ አይረሳውም። ሳይበቀልህ አይተውህም። ሳይበቀልህ ብትሞትበት በቁጭት ተቃጥሎ ሊሞት ይችላል። ክብር ውድ ነው። አደገኛ ዋጋ ያስከፍላል። ስለዚህ
አብሮ ለመኖር የመጀሪያው ጥበብ መከባበር ነው!
ሲባል አለምክንያት አይደለም።
ዲያቆን
ዳንኤል ክብረት ከአንዲት ከንፈሮችዋ ከሚያምሩ ሴት ጀርባ ባንዴራ ይዞ ቆሞ፣ ቅዱስ ሳጥናኤልን መስሎ "መንጋ" የተባለ አሳፋሪ እና አስጸያፊ ግጥም ሲያስነብብ በውነት ለኢትዮጵያ አንድነት በጎ መስራቱ ነው? የኦሮሞን ህዝብ በደብተራ ቅኔ በመስደብ፣ በአሽሙር በማሽሙዋጠጥ ምን ለማትረፍ ነበር የፈለገው? ብሽሽቅ? የኦሮሞን አንገት ማስደፋት? ማሸማቀቅ? ያውም
አብይ እና
ሳህለወርቅን እዚያው አስቀምጦ!?
እና ምን አተረፈ?
ይኸው ውጤቱ ታየ።
አብይ ከመምጣቱ በፊት የኦርቶዶክስ ጳጳሳትን እንኩዋ ለማስታረቅ ያልሞከረ ሰው በምን መለኪያ የአብይ አማካሪ ሊሆን እንደቻለ በፍጹም ሊገባኝ አልቻለም። እንግዲህ ነገም በዚያችው የደብተራ ችሎታው ማሽሙዋጠጡን ከቀጠለ ሌላ ሞት ይጠራል። ሌላ ቤተክርስትያን ይቃጠላል። ሌላ የማያቁዋርጥ ትኩሳት። እና አፍሪቃ ቀንድም አብራ በወላፈኑ ትጠበሳለች!!
እና ጠላቶቼ ሆይ!
የኢትዮጵያ ሰላም ነቀርሳ ጃዋር ሳይሆን የዲያቆኑ አይነት ትምክህተኛ አስተሳሰቦች ናቸው። እንዲህ በቀጥታ መግለጼ ከጃዋር ጋር ማህበር መስርቼ አይደለም። ከጃዋር ጋር ከአንድም ሁለት ጊዜ ተጋጭቼ አውቃለሁ። ችግሮች እንዳሉበት አውቃለሁ። እውነቱን ግን አልደብቅም። ጃዋር የፖለቲካ ነጋዴ አይደለም። ብልጣብልጥ ጮሌ አይደለም። ከታች ከመሰረቱ ጀምሮ ከህዝቡ ጋር እየታገለ እዚህ የደረሰ ነው። የነገውን አላውቅም። እስከዛሬ ግን ጃዋር ለጥቅም ሲል ከአቁዋሙ ሲንሻፈፍ አልታየም።
በውነቱ እኔ በአብይ አህመድም ተስፋ አደርጋለሁ። በፍጹም ጨካኝ ልብ ሊኖረው አይችልም። እስካሁን ተንኮል አላየሁበትም። እንደማንኛውም ፖለቲከኛ መታየትና አድናቆት ሊወድ ይችላል። ይሄ የሰው ጠባይ ነው። ነፍሱ ደግሞ ለስነ-ጥብበ ያጎበደደች ሰለሆነች ሊጋነንበት ይችላል። አብይ አህመድ ያበደ የራሱ አለም አለው። ደግ ልቡ ይታየኛል። እንደልቡ ነው። የስልጣን ጥማት አለው ብዬ ግን በፍጹም አላምንም። አብይ አንድ ማለዳ ድንገት ብድግ ብሎ፣
የራሳችሁ ጉዳይ! ዙፋኑ ያውላችሁ! አትጨቅጭቁኝ!
ብሎ ቤተመንግስቱን ጥሎ አሜሪካ ቢሄድ አይደንቀኝም።
ጃዋር እንዲገደል አብይ ተባብሮአል!
የሚል ኦሮምኛ ግን ውሃ አያነሳም። ማመን አልችልም። ማስረጃ እፈልጋለሁ።
እስካሁን እንደተከታተልኩት እና ያለኝ መረጃ እንደሚጠቁመኝ የአብይን የፓርላማ ንግግር እንደ ጥሩ አጋጣሚ በመጠቀም ጃዋርን ለመግደል ሴራ የሸረቡ ሰዎች ይኖራሉ. . .እነማን ናቸው?
ዋቃ ጉራቻ ያውቃል!!