"የኢትዮጵያ የባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ አገልግሎት ድርጅት ከሚያስተዳድራቸው አንዱ የሆነው መርከብ ድርጅት፣ የኤርትራ ጭነቶችን ወደ ህንድና ቻይና በማጓጓዝ ላይ እንደሚገኝ አስታወቀ፡፡ ሁለቱ አገሮች እንደ አዲስ ግንኙነታቸውን ከጀመሩ ወዲህ፣ ከ35,300 ቶን በላይ የዚንክ ማዕድን እንዳጓጓዘ ድርጅቱ አስታውቋል፡፡
በሦስት የኢትዮጵያ መርከቦች አማካይነት የዚንክ ማዕድን ወደ ህንድና ቻይና እንዳጓጓዘ ከድርጅቱ የተገኘው መረጃ ያስረዳል፡፡ በድርጅቱ መርከቦች ከተጓጓዙት ማዕድኖችም የኢትዮጵያ ንግድ መርከብ 1.1 ሚሊዮን ዶላር ማግኘቱ ተጠቁሟል፡፡
ቅዳሜ መስከረም 10 ቀን 2012 ዓ.ም. መግለጫ የሰጠው ድርጅቱ መቐለ፣ ፊንፊኔና ጋምቤላ በተሰኙት መርከቦች አገልግሎት መስጠቱን አስታውቋል፡፡
የባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ አገልግሎት ድርጅት ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሮባ መገርሳ፣ ለኤርትራ እየቀረበ የሚገኘውን የመርከብ አገልግሎት ጨምሮ የተቋሙን አፈጻጸም በማስመልከት ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡
https://www.ethiopianreporter.com/index ... icle/16832