ጋዜጠኛ ሳዲቅ ይቀጥልና ማህበረሰቡ ግዜያዊ ማስታገሻዎችን፣ የግዜያዊ ችግሮችን መፍትሔ ለማግኘት ይጣር እንጂ የሚፈጸምበትን አስተዳደራዊ በደል ለማስቀረት በመደራጀት ላይ አይደለም። ለጉዳዩ ተጠያቂ የአዲስ አበባ ከንቲባ ሆኖ ሳለ በምጽዋት የሚሰጥ ፖለቲካዊ ጥቅም ያለ እስኪመስል ድረስ «ለውጡን ለማደናቀፍ የተሰገሰጉ አካላት» ብሎ ምክንያት መስጠቱ ፖለቲካዊ-ሚስኪንነት ነው።ምላሹ መሆን ያለበት ተነስ፣ ተደራጅ፣ እራስህን ለምርጫ ኮሮጆ አዘጋጅ ነው ይላል።
በዘመነ ታከለ ኡማ አዲስ አበባ ውስጥ አራት መስጊዶች ፈረሱ፤ ይህ ደግሞ ታከለ ኡማ በጊዜያዊነት በከንቲባነት ተቀምጦ ሳለ ነው። ታከለ ኡማ እስከ ምርጫ ደርሶ ምርጫን ቢያሸንፍና ህጋዊ እውቅናን አግኝቶ ለአመታት ከንቲባ ሆኖ ቢቀጥልስ? ይህ ታስቦበታልን?
በዚህ ተንኳሽ (provocative) ሙከራ ምን ለመስራት ታስቧል? ሙስሊሙ ማህበረሰብ መካከል እርቀሰላም ሰፍነ፣ ለአያሌ አመታት መጅሊስን አስመልክቶ ሲጠየቅ የነበረው ጥያቄ ፈር ያዘ ሲባል ማህበረሰብን ለጸብ የሚጋብዝ ተግባር መፍጸሙ በአገሪቷ ሰላምና መረጋጋት ላይ የተቃጣ ስንኩል ተግባር አይደለምን ሲልም ይጠይቃል።
ግዜው የአመት በዓል ነ፤ ኢድ ከቀናት በኋላ ይውላል። አዲሱ የመጅሊስ አመራርና ሌሎች ተሰሚነት ያላቸው ሰዎች ለሐጅ ወደ መካ አቅንተዋልዩ ብዙ ሰዎች ኢድን ከቤተሰብና ከዘመድ ጋር ለማክበር ወደ ገጠር አቅንተዋል።
መስጊድን ከኢድ በፊት ማፍረስ አጋጣሚ ነው ወይስ ለውጥ መጣልኝ ብሎ ተስፋ የሰነቀው ሙስሊም ማህበረሰብ በቁጭትና በምሬት እንዲብሰለሰል የማድረግ ሴራ ? በማለት የታከለ ኡማ ኬላ የለሽ (free pass) ውሳኔ ይቀጥላል ሲል ተችቷል።
ከንቲባው የጠቅላይ ሚንስትሩ ፖለቲካዊ ምሶሶም ስለሆነ እምብዛም ላይሰጋ ይችላል። ከንቲባውን በአንክሮ ለተመለከተ ደግሞ ረጅም ፖለቲካዊ ምኞች ያለው ይመስላል። ከምእራብ አገራት በተኮረጁ ፖለቲካዊ እንቅስቃሴዎቹ ለወደፊቱ አገር ለመምራት የምርጫ ዘመቻ ላይ ያለ ወጣት ፖለቲከኛ ይመስላል። ‹የልብን አድርሶ ይቅርታ› እንደሚባለው ሰሞኑን የፎቶ ግርግር ( photo op) ፈጥሮ፣ ከምእምናን ጋር ተቃቅፎ ነገሩን ለማበራረድ ቢሞክር አይገርምም ብሏል።
ጋዜጠኛ ሳዲቅ ይቀጥላል፤ ጥያቄው ይህንን ለቀጣዩ የከንቲባነት ምርጫ ዘመቻ በተግባር «በገድሎ ማዳን» ትርክት የሚንቀሳቀሰውን ከንቲባ እንዴት አድርጎ በድምጽ መቅጣት ይቻላል? የሚለው ሊታሰብበት ይገባል ያለው ጋዜጠኛው አዲስ አበባ የፖለቲካ ካፒታል ናት ብሏል።
የአገሪቷ ፖለቲካ አዲስ አበባ ወደነጎደችበት ይነጉዳል በሚል ስጋት እነ መለስ ዜናዊ በ1997ቱ ምርጫ የፈጸሙት ወንጀል አይዘነጋም፤ ሌሎችም የፖለቲካ ሐይላት ባለ በሌለ ሐይላቸው አዲስ አበባን ለመቆጣጠር ሲረባረቡ ይስተዋላል ሲል ጽሁፉን ይቀጥልና ተቃዋሚዎቹ ስላቅ በሚመስል መልኩ ገና በ«ማ» እየተጨቃጨቁ ነው፤ ስለዚህ በቀጣዩ ምርጫ 23ቱ ወረዳዎች የማን ይሆናሉ? የእምነት ተቋም ፈረሰብኝ እሮሮው ወደ ምርጫ ኮሮጆ ሲያቀና ብቻ ነው የተሻለ መልስ የሚገኘው ብሏል።
መማረሩ፣ ለውጡን ሊያደናቅፉ የሚሹ ሐይላት አፈረሱብን እያሉ ምክንያት መስጠቱ ያብቃ፤ ግርማ-ሞገስ ያለው ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ ይጀመር፤ ያኔ ምድረ-አስመሳይ ፖለቲከኛ ጠብ-እርግፍ ሲል ይታያል፤ ልብ ያለው ልብ ይበል በማለት ፁሁፋን ያጠናቅቃል።


