በደሴ ከተማ የሰዓት እላፊ ገደብ ተቀመጠ
---------------------
ነሃሴ 4/2013 (ዋልታ) - በደሴ ከተማ አስተዳደር ወቅታዊውን ሁኔታ መሰረት ያደረገ የሰዓት እላፊ ገደብ አስቀመጠ፡፡
ነባራዊው የከተማው ሁኔታ ከወትሮው በተለየ የከተማችንን ህዝብ ልዩ ክትትልና ድጋፍ የሚጠይቅ ነው ብሏል አስተዳደሩ።
ሆኖም ለከተማው ህዝብ ሁለንተናዊ ደህንነት ሲባል በሰዓት የተገደበ የተሽከርካሪና የሰው የእንቅስቃሴ ገደብ አስቀምጧል።
በዚህም አስተዳደሩ የከተማዋ ነዋሪዎች ከምሽቱ 2:00 ጀምሮ ከተፈቀደላቸው የፀጥታ አካላት ውጭ የትኛውም ዓይነት እንቅስቃሴ የተከለከለ ነው ብሏል።
ከተፈቀደላቸው የፀጥታ ተቋማትና የጤና ተቋማት ተሽከርካሪዎች ውጭ ከምሽቱ 2:00 ሰዓት ጀምሮ እንቅስቃሴአቸው እንዲገደብ ተወስኗል።
እንዲሁም የሶስት እግር ባጃጅ ተሽከርካሪዎች እንቅስቃሴ እስከ ምሽቱ 12:00 ሰዓት ብቻ እንዲሆን የተወሰነ መሆኑን አስታውቋል፡፡
ውሳኔው ከዛሬ ነሀሴ 04/2013 ዓ.ም ጀምሮ በከተማው ተግባራዊ የሚደረግ ሲሆን ሁሉም የከተማው ነዋሪዎችም በተለመደው አግባብ ለሁሉን አቀፍ ትብብር እንዲያዘጋጁ ከተማ አስተዳደሩ ጥሪውን አቅርቧል፡፡
Please wait, video is loading...