የአሜሪካው ኢሳት ቴሌቪዥን ቦርድ የ264 ሺ ዶላር ክስ ቀረበበት
July 1, 2021
Tamerat Hailu
ለረዥም ዓመታት በትግል ሚዲያነት የሚታወቀውና አሁን ለመጣው ለውጥ የጎላ ሚና ስለመጫወቱ በሚታመነው በኢሳት ቴሌቪዥን ቦርድ አመራሮች መሀከል የተፈጠረው አለመግባባት ወደ ፍርድ ቤት ስለመድረሱ እየተነገረ ነው፡፡
ወደ አዲስ አበባ በገባውና ኢሳት ቴሌቪዥን ቦርድና በአሜሪካ ሀገር በበጎ አድራጎት ድርጅትነት ተመዝግቦ የሚንቀሳቀሰውን ቦርድ እየመራ ባለው ቦርድ አመራሮች መሀከል በተፈጠረ አለመግባባት ሳቢያ የአዲስ አበባው ቦርድ አመራሮች አማካይነት በአሜሪካ ሀገር ክስ ፋይል መከፈቱ ተሰማ፡፡
በአሜሪካው የኢሳት ቦርድ አመራሮችና በሀገር ቤት ባለው የኢሳት አመራሮች መሀከል የተፈጠረው አለመግባባት ኢሳት ወደ ሀገር ቤት ገብቶ ስራ ከጀመረበት ካለፉት ሶስት ዓመታት ጀምሮ የተከሰተ ሲሆን ኢሳት ለውጡን ተከትሎ ወደ ሀገር ቤት ቢገባም የህዝቡን የዲሞክራሲና የፍትሕ ጥያቄ ወደ ጎን በመተው የለውጥ አመራሩን ብቻ ወደ መደገፍ በማምራቱ ሳቢያ አለመግባባቶች ጎልተው ስለመውጣታቸው ይነገራል፡፡
ወደ ሀገር ቤት የገባውና በአቶ አንዳርጋቸው ፅጌ የሚመራው የኢሳት ቦርድ ኢሳትን ኃላፊነቱ በተወሰነ የግል ኩባንያ ስም ህጋዊ መሠረት ለማስያዝ በግለሰቦች ባለቤትነት ማስመዝገቡ የአሜሪካውን የኢሳት ቦርድ እንዳላስደሰተ ታውቋል፡፡ ይህንኑ ተከትሎም የአሜሪካው ኢሳት ቦርድ የቴሌቪዥኑን የባንክ ሂሳብ፤ የዩቲዩብ እና የፌስቡክ አካውንት በመያዝ ራሱን ከሀገር ቤቱ ኢሳት መነጠሉን ያሳወቀ ሲሆን በቅርቡም በዶ/ር ሰለሞን ረታ የሚመራ 10 አዳዲስ የቦርድ አባላትን በመምረጥ የቀድሞ የኢሳትን ዓላማን ማለትም የህዝብ ድምፅነት ለመቀጠል እንቅስቃሴ እንደሚያደርግ በኢሳት የአሜሪካ ስቱዲዮ በቦርዱ የህዝብ ግንኙነት ሀላፊ አቶ ጌታቸው አብዲ የተነበበው የአቋም መግለጫ ያሳያል፡፡
በአሜሪካው የኢሳት ቦርድ አመራሮች የተወሰደውን ለውጥና እንቅስቃሴ የተቃወመው የአዲስ አበባው ኢሳት ቦርድ አመራር ከአዲሱ የፕሬስ አዋጅ መፅደቅ ማግስት ራሱን ከግል ሚዲያነት ወደ ‹በጎ አድራጎት መገናኛ ብዙሃንነት› መለወጡን ገልፆ አዳዲስ የቦርድ አባላትን መምረጡን ይፋ አድረጓል፡፡
የአሜሪካው ኢሳት ቦርድ አመራሮች ጣቢያው የፋይናንስ እጥረት እንዳጋጠመው በመጥቀስ ከዓመት በፊት ከአየር ላይ እንዲወርድ በማድርግ ጎ ፈንድ ሚ በተባለው ህዝባዊ ገንዘብ ማሰባሰቢያ ዘዴ 264 ሺ ዶላር መሰብሰቡን በመጥቀስ ይህ ገንዘብ ለነባሩ የኢሳት ቦርድ ሊመለስ ይገባል በማለት የሀገር ቤቱ ኢሳት ቦርድ በአሜሪካ ፍርድ ቤት ክስ መስርቷል፡፡ የአዲስ አበባው ኢሳት ቦርድ ከዚህ በተጨማሪም የአሜሪካውን የኢሳት ቦርድ የሚመሩት ዶ/ር ሰለሞን የኢሳትን የዩቲዩብና የፌስ ቡክ አካውንቶች እንዲመልሱ እንዲታዘዝላቸው በክሳቸው ላይ መጠየቃቸውን ምንጮች ተናግረዋል፡፡
በዶ/ር ሰለሞን የሚመራው የአሜሪካው ኢሳት ቦርድ የመጀመሪያ ደረጃ መቃወሚያውን ለፍርድ ቤቱ ማስገባቱ ታውቋል፡፡
https://kumnegermedia.com/amharic/የአሜሪካ ... የ264-ሺ-ዶላ/