

Source:
Amhara Mass Media Agency
በየቀኑ 3 መቶ ያህል አማሮች ከሱዳን በመተማ በኩል ወደ ሀገራቸው እየተመለሱ እንደሚገኝ ተገለጸ፡፡
ባሕር ዳር፡ ታኅሣሥ 27/2013 ዓ.ም (አብመድ) አማሮቹ በሱዳን ትንኮሳ እየተፈጸመባቸው እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
በሱዳንና በኢትዮጵያ ድንበር አካባቢ የተገኘው የአልጀዚራ ዘጋቢ እንደገለጸው በሱዳን የተለያዩ ከተሞች ይሠሩ ወይም ይኖሩ የነበሩ አማሮች በመተማ በኩል ወደ ሀገራቸው እየተመለሱ ነው፡፡
አማሮቹ በሁለቱ ሀገራት ድንበር አካባቢ ያለው ውጥረት ስጋት እንዳሳደረባቸው እና ቤተሰቦቻቸውን እና ንብረታቸውን በመያዝ በመተማ በኩል ወደ ሀገራቸው እየተመለሱ መሆኑን ዘገባው አመላክቷል፡፡
አልጀዚራ ያነጋገራቸው እና ድንበር አቋርጠው መተማ የደረሱ አማሮች በሰጡት አስተያየት ይኖሩባቸው በነበሩ አንዳንድ የሱዳን ከተሞች ተለይተው ትንኮሳ እና በንብረታቸው ላይ ጥቃት እንደተፈጸመባቸው ተናግረዋል፡፡
የመተማ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ አንዳርጋቸው ሞላ በሱዳን አማሮች እየተፈናቀሉ ወደ ሀገራቸው እየተመለሱ እንደሆነ እና ጉዳዩ አሳሳቢ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በሁለቱ ሀገራት ድምበር አካባቢ ያለው ችግር የዜጎችን ህይወት የሚያመሳቅል መሆን እንደሌለበት እና ወቅታዊ ችግሩ ተፈትቶ የሀገራቱ ሕዝቦች የቆየ ግንኙነታቸው በዘላቂነት እንደሚቀጥልም ተናግረዋል፡፡
ከሱዳን ወደ ሀገራቸው እየተመለሱ ያሉት አማሮች እንደተናገሩት የሱዳን ጦር የኢትዮጵን ድምበር አቋርጦ በመግባት በአርሶ አደሮች እና በባለሃብቶች ንብረት ላይ ጥቃት ማድረሱን ተከትሎ እነሱም የጥቃት ሰለባ እንሆናለን የሚል ስጋት አድሮባቸዋል፡፡
በየማነብርሃን ጌታቸው